Quantcast
Channel: Ethiopian Legal Brief
Viewing all articles
Browse latest Browse all 992

የእምነት ቃል —የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0

በወንጀል ተጠርጣሪ ግለሰብ በምርመራ ሂደት ወይም ደግሞ ተከሳሽ በክሱ ሂደት የራሱን አጥፊነት በመቀበል የሚሰጠው ቃል

አንድ ተጠርጣሪ ወይም ተከሳሽ በምርመራ ሂደትም ሆነ ክስ ከቀረበበት በኃላ ክሱን ለሚሰማው ፍርድ ቤት የሚሰጠው የእምነት ቃል በሕግ ተቀባይነት ካላቸው የማስረጃ ዓይነቶች ውስጥ የሚካተት መሆኑ በወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 27፣ 35 እና 134 ድንጋጌዎች ተመልክቷል፡፡ ተጠርጣሪው ወይም ተከሳሹ የዚህ ዓይነቱን የእምነት ቃል የሚሰጠው የራሱን አጥፊነት አምኖ በመቀበል እንደሆነ የሚገመት በመሆኑ ሌሎች ተጠርጣሪዎች፣ ተከሳሾች ወይም ማናቸውም ሌላ ሰው በወንጀሉ አደራረግ ውስጥ ተሳትፎ የነበራቸው ስለመሆኑ ወይም ስላለመሆኑ በእምነት ቃሉ ውስጥ የሚገልጻቸው ፍሬ ነገሮች ምናልባት ለቀጣይ ምርመራ ፍንጭ ሊሰጡ ይችሉ ይሆናል ከሚባል በቀር በማናቸውም ሰው ላይ አሉታዊም ሆነ አዎንታዊ ሕጋዊ ውጤት ሊያስከትሉ የሚችሉ ተደርገው ሊወሰዱ የሚችሉበት የሕግ አግባብ የለም፡፡

በሌላ አነጋገር አንድ ተጠርጣሪ ወይም ተከሳሽ በምርመራ ሂደትም ሆነ ክሱን ለሚሰማው ፍርድ ቤት የሚሰጠው የእምነት ቃል ውጤት በራሱ በቃል ሰጪው ላይ ተወስኖ የሚቀር ከመሆኑ ውጪ ወደሌሎች ተጠርጣሪዎች ወይም ተከሳሾች ሊተላለፍ የሚችል አለመሆኑን ከላይ ከተጠቀሱት ድንጋጌዎች አነጋገር እና ይዘት መገንዘብ የሚቻል ከመሆኑም በላይ ወንጀሉን የፈጸሙት በጋራ ወይም በመተባበር መሆኑን በማመን አንደኛው ተከሳሽ የሚሰጠው የእምነት ቃል ወንጀሉን አልፈጸምኩም በማለት ክዶ በሚከራከረው ሌላኛው ተከሳሽ ላይ ሕጋዊ ውጤት ሊያስከትል የማይችል ስለመሆኑ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት በመዝገብ ቁጥር 94450 በ25/07/2006 ዓ.ም. የሰጠው አስገዳጅ የሕግ ትርጉም በተያዘው ጉዳይ ላይ ተፈጻሚነት ያለው መሆኑን ተገንዝበናል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 96310 ቅጽ 17፣[1] ወ/መ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 27፣35 እና 134

በወንጀል ጉዳይ በወ/መ/ሕ/ሥ/ሥ/ቁ. 134(1) እንደተደነገገው ተከሣሹ የተከሰበበትን የወንጀል ክስ ይዘት በሚገባ ተረድቶ አድራጐቱን እንደቀረበበት የወንጀል ክስ ዝርዝር መፈፀሙን አምኖ የእምነት ቃል በሰጠ ጊዜ ይህ የእምነት ቃል ለቀረበበት የወንጀል ክስ ማስረጃ ሆኖ በዚሁ ማስረጃ መሠረት የጥፋተኝነት ውሣኔ መስጠት የሚቻልበት ሥርዓት ተደንግጓል፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ አኳኋን ተከሣሹ የሚሰጠው የእምነት ቃል በማስረጃነቱ ተይዞ የሚሰጠው የጥፋተኛነት ውሣኔ ውሣኔውን በሰጠው ፍ/ቤቱ ብቻ ተወስኖ የሚቀር አይደለም፡፡ በዚህ ውሣኔ ቅሬታ የተሰማው ወገን በህገ-መንግስቱም አንቀጽ 20(6) ሆነ በዝርዝር በወ/መ/ሕ/ሥ/ሥ/ሕጉ መሠረት ከታች ወደ ላይ በይግባኝ የመከራከር መብቱን ለማስጠበቅ የይግባኝ አቤቱታ የሚያቀርብበት ሥርዓት ተዘርግቷል፡፡

በዚህ መሠረት በይግባኝ በሚቀርበው መከራከሪያ ነጥብነቱ እንደ ወ/መ/ሕ/ሥ/ሥ/ቁ. 134(1) ድንጋጌ አነጋገር የወንጀሉን አድራጐት ለመፈፀሙ የእምነት ቃል አልሰጠሁም፤ ነገር ግን እንዳመንኩ ተደርጎ ጥፋተኛ ነህ ተብያለሁ በማለት ቅሬታ የቀረበ እንደሆነ ተከሳሹ ተላልፎታል በሚል የተጠቀሠበት ድንጋጌ ሥር የተቋቋመውን የወንጀል ዝርዝር ተከሣሹ በአፈፃፀሙ ረገድ የሰጠውን ዝርዝር የአፈፃፀም ሁኔታ በማገናዘብ በእርግጥም እንደ ክሱ የወንጀሉን አድራጐት ፈጽሞታል ወይስ አልፈፀመውም የሚለውን ለመለየት ተከሣሹ ሰጠ የተባለው ዝርዝር የእምነት ቃል በመዝገቡ ላይ ሠፍሮ ካልተገኘ በቀር የበላይ ፍ/ቤቶች ተገቢውን ዳኝነት ለመስጠት አያስችላቸውም፡፡

ሰ/መ/ቁ 77842 ቅጽ 14፣[2] ወ/መ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 134/2/

በወንጀል የተከሰሰ ሰው ጥፋተኛ ተብሎ የሚቀጣው በወ/መ/ሥ/ሥ/ሕግ ቁጥር 134(1) መሠረት በሰጠው የእምነት ቃል መሰረት ከሆነ ፍርድ ቤቶች ተከሳሹ ከሰጠው የእምነት ቃል ውስጥ ተከሳሹን የሚጠቅመውን ክፍል በመተው፤ በዕምነት ቃሉ ያላስመዘገበውን ፍሬ ነገር መሰረት በማድረግ ቅጣት ሊያከብዱ አይገባም፡፡

ሰ/መ/ቁ 96954 ቅጽ 16[3]

[1] አመልካች አቶ ጉዲና ለማ ገዛኸኝ እና ተጠሪ የደቡብ ብ/ብ/ሕ/ክ/መንግስት የስ/ፀ/ሙስና ኮሚሽን ዐ/ሕግ ህዳር 26 ቀን 2007 ዓ.ም.

[2] አመልካች አቶ ሳሚ ሁሴን እና ተጠሪ የፌደራል ዐቃቤ ህግ ታህሣስ 03 ቀን 2005 ዓ.ም.

[3] አመልካች ዘፈሩ ወልደ ትንሣኤ አብርሃ እና ተጠሪ የፌዴራል ዐቃቤ ህግ ሚያዚያ 24 ቀን 2006 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

Viewing all articles
Browse latest Browse all 992

Trending Articles



<script src="https://jsc.adskeeper.com/r/s/rssing.com.1596347.js" async> </script>