ፍቺ
በይርጋ ቀሪ የማይሆን፣ ክስ ለማቅረብ በህግ የጊዜ ወሰን ያልተቀመጠለት የመብት ጥያቄ
አደራ
ወራሾች በአደራ የተያዘ የሟች ንብረት ለማስመለስ የሚያቀርቡት ክስ በይርጋ አይታገድም፡፡
ሰ/መ/ቁ. 48048 ቅጽ 10፣[1] ፍ/ህ/ቁ. 2779፣ 2781፣ 2989(1)
የውርስ ሀብት ክፍፍል
የውርስ ክፍያ ጊዜን በተመለከተ የፍ/ብ/ሕጉ በአንቀጽ 1062 ስር የደነገገ ሲሆን የድንጋጌው ይዘትም ውርሱ በተጣራ ጊዜ በማናቸውም ጊዜ ቢሆን እያንዳንዱ የጋራ ወራሾች ውርሱን እንከፋፈል ብለው ለመጠየቅ እንደሚችሉ መደንገጉን የሚያሳይ ነው፡፡ በፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1060 ድንጋጌ ስር ደግሞ የውርስ አከፋፈል እስካልተፈፀመ ድረስ ውርሱ በወራሾች መካከል ሳይነጣጠል እንደሚቆይ ተመልክቷል፡፡ በመሆኑም ወራሽ የሟች ወራሽቱን በሕጉ በተመለከተው የጊዜ ገደብ አረጋግጦ ከቆየ በኋላ የሚያቀርበው የውርስ ንብረት የክፍፍል ጥያቄ በፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1000/1/ እና /2/ ስር በተመለከተው የይርጋ ድንጋጌ የሚታገድ ሳይሆን በፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1062 ድንጋጌ መሠረት በማናቸውም ጊዜ የሚቀርብ ነው፡፡
ሰ/መ/ቁ. 38533 ቅጽ 10፣[2] ፍ/ህ/ቁ. 1000(1) እና (2)፣ 1060
የመፋለም ክስ
የማይንቀሳቀስ ንብረት የመፋለም ክስ በይርጋ ቀሪ አይሆንም፡፡ ከባለቤትነት መብት ጋር ተያየዥነት ያላቸው ነገር ግን ከመፋለም መብት ውጪ ያሉ ሌሎች ክሶች እንደሚጠየቀው መፍትሔ እና ለክሱ ምክንያት እንደሆነው ጉዳይ ዓይነት /ጋብቻ፣ ውርስ፣ ሽያጭ፣ ወዘተ…/ በሌሎች ልዩ የይርጋ ህግ ደንቦች የሚተዳደሩ ናቸው፡፡
ሰ/መ/ቁ. 43600 ቅጽ 10[3]
የንግድ ማህበር እንዲፈርስ
የንግድ ማህበር ይፍረስልኝ ጥያቄ በውል ከተቋቋመ የማህበርተኝነት መብት የሚመነጭ እና በማህበሩ እንቅስቃሴ ሂደት የሚፈጠሩ የተለያዩ ችግሮችን መሰረት አድርጐ የማህበሩ ህልውና እስካለ ድረስ በማንኛውም ጊዜ ሊቀርብ የሚችል ነው ከሚባል በቀር በታወቀ የይርጋ ጊዜ የሚታገድ ስለመሆኑ የንግድ ሕጉ ድንጋጌዎች አያመለክቱም፡፡ የማህበር ይፍረስልኝ ክስ በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር. 1845 በተመለከተው ጠቅላላ የይርጋ ጊዜ ይታገዳል ሊባል ይችል የነበረውም የይፍረስልኝ ጥያቄው የቀረበው ተለይቶ በታወቀ ቀን የተፈጠረ ክስተትን ጠቅሶ ወይም መሰረት አድርጐ ቢሆን ኖሮ እና ክሱ የቀረበው ክስተቱ ከተፈጠረ አስር ዓመት ካለፈው በኋላ ቢሆን ኖሮ ነው፡፡
ሰ/መ/ቁ. 94278 ቅጽ 17፣[4] ን/ህ/ቁ. 218(1)፣ 542(!)፣ ፍ/ህ/ቁ. 1835
[1] አመልካች ወ/ሮ ገብርኤላ ኒካላ ቶማስ ናክሶ ተጠሪ የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ ሐምሌ 22 ቀን 2002 ዓ.ም.
[2] አመልካቾች እነ ወ/ሮ ጽጌ ወልደመስቀሌ /6 ሰዎች/ እና ተጠሪ አቶ ስዩም ክፍሌ ህዳር 08 ቀን 2002 ዓ.ም.
[3] አመልካች ዳዊት መስፍን እና ተጠሪ የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ ጥር 5 ቀን 2002 ዓ.ም.
[4] አመልካች አቶ ሐሰን መሐመድ እና ተጠሪ ማጂ አግሮ ፎረስትሪ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ስራ አስኪያጅ ህዳር 11 ቀን 2007 ዓ.ም.
Filed under: Articles, Case Comment
