Quantcast
Channel: Ethiopian Legal Brief
Viewing all articles
Browse latest Browse all 992

የአስተዳደራዊ ድንጋጌዎች ህጋዊነትና ህገ መንግስታዊነት

$
0
0

ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግር ሲፈጠር መፍትሔ የመሻት ቀዳሚ ኃላፊነት የተጣለባቸው በየዘርፉ የተቋቋሙ የአስተዳደር መ/ቤቶች ናቸው፡፡ ከትምህርት አሰጣጥ ወይም ጋር ጥራት ጋር የተያያዘ ወይም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ ችግር ሲከሰት የትምህርት ሚኒስቴር እንቅስቃሴ ይጀምራል፡፡ በጉምሩክ ህግ አፈጻጸም አቤቱታዎች ሲጎርፉ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን መፍትሔ ያፈላልጋል፡፡ በግንባታ ላይ የተሰማሩ ሠራተኞች ጉዳት ሲደርስባቸው የሠራተኛ ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የሥራ ላይ አደጋዎች እንዳይከሰቱ ትኩረት ሰጥቶ ስራ ይጀምራል፡፡ ችግሮችን ለመቅፍ መላ መዘየድ ችግር የለውም፤  እንዲያውም ይበረታታል፡፡

ይሁን እንጂ በአንድ አገር ውስጥ በየጊዜው የሚፈጠሩ ችግሮች ሊቀረፉ የሚገባው በህግና በህገ መንግስት ማዕቀፍ ውስጥ ነው፡፡ ከፊል ጉዳዮች የተወካዮች ም/ቤትን ጣልቃ ገብነት ይሻሉ፡፡ የአስተዳደር መ/ቤቶች ችግር ፈቺነት አቅም በህግ ከተፈቀደላቸው ስልጣን በላይ ሊለጠጥ አይችልም፡፡ አዋጅ ሊመልሰው የሚገባውን መመሪያ ከቀደመው መ/ቤቶች ችግር ፈቺ መሆናቸው ቀርቶ ችግር ፈጣሪ ይሆናሉ፡፡ የአስተዳደር ድንጋጌዎች መመዘኛ አስፈላጊነትና ጠቀሜታ ብቻ ሳይሆን በዋናነት ህጋዊነት ነው፡፡ የቄሳርን ለቄሳር እንዲሉ ተወካዮች ሊመክሩበትና ሊፈቱት የሚገባውን ችግር ተሿሚዎች በመመሪያ ለመቅረፍ መሽቀዳደም የለባቸውም፡፡ የሚከተለው አጭር ዳሰሳ መመሪያ እና ደንብ እያስከተሉት ያለውን የህጋዊነትና ህገ መንግስታዊነት አደጋ በአጭሩ ያስቃኛል፡፡

 1. የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የአምልኮ ስርዓት

በትምህርት ተቋማት የአምልኮ ስርዓትን በሚመለከት የትምህርት ሚኒስቴር በ2000 ዓ.ም. መመሪያ አውጥቷል፡፡[1] መመሪያው ከመዋዕለ ህጻናት እስከ ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ድረስ በሁሉም የትምህርት ተቋማት ተፈጻሚ የሚሆነውን የአምልኮ፣ የአለባበስ እና የአመጋገብ ስርዓት ይደነግጋል፡፡ በአንቀጽ 6.2 እስከ 6.6 ድረስ ከተፈቀዱና ከተከለከሉ ተግባራት መካከል እንደ ቅደም ተከተሉ የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡

  • 2 የተማሪ ደንብ ልብስ በማያስፈልጋቸው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እንደሁኔታው በወርክሾፕ፣ በላቦራቶሪ፣ ወይም በህክምና ትምህርት ተቋማት ሙያው ወይም ስልጣናው የሚፈልገው አይነትና የአንዱን ወይም የሌላውን እምነት የማይጋፋ የአለባበስ ስርዓት መከበር ይኖርበታል፡፡
  • 3 የእስልምና እምነት ተከታይ ሴት ተማሪዎች ከዩኒፎርም ጋር የሚመሳሰል “ሂጃብ” ማድረግ ይችላሉ፤ ከሂጃብ በቀር ሙሉ ጥቁር ልብስ ሙሉ በሙሉ ፊትንም ጨምሮ የሚሸፍን ወይም “ኒቃብ” በትምህርት ተቋማት መልበስ አይፈቀድም፡፡
  • 4 የክርስትና እምነት ተከታይ መነኮሳት፤ መነኮሳያይት እና ካህናት እንዲሁም የእስልምና ተከታይ ሼኮች ብቻ በትምህርት ተቋማት ቆብ ሊያደርጉ ወይም ሻሽ ሊጠመጥሙ ይችላሉ፡፡
  • 5 በተራ ቁጥር 6.2፤ 6.3፤ 6.4 የተጠቀሱት እንደተጠበቁ ሆነው፤ የትምህርት ተቋማት በሚያዘጋጁት ክብረ በዓል ወይም ተመሳሳይ ጉዳዮች ምክንያት በተቋሙ አስተዳደር ሃይማኖታዊ አለባበሶች ካልተፈቀዱ በስተቀር በማንኛውም መልኩ የማንኛውንም የሃይማኖት የአለባበስ ስርዓት በትምህርት ተቋማት መልበስ አይፈቀድም፡፡
  • 6 በተራ ቁጥር 6.2፤ 6.3፤ 6.4 የተጠቀሱት እንደተጠበቁ ሆነው፤ በተለየ ሁኔታ የትምህርት ተቋሙ አስተዳደር (በሀዘን፣ በህመም ወዘተ) ከሚፈቅደው በስተቀር ተማሪዎች በመማሪያ ክፍል ውስጥ ነጠላ፣ ጋቢ ወዘተ… መልበስ ሻሽ መጠምጠምና ቆብ ማድረግ የተከለከለ ነው፡፡

የትምህርት ሚኒስቴር መመሪያውን ለማውጣት የስልጣኑን ምንጭ በጊዜው ፀንቶ የነበረውን የኢትዮዽያ ፌደራላዊ ዲሞከራሲያዊ ሪፐብሊክ አስፈፃሚ አካላትን ስልጣንና ተግባር ለመወሰን የወጣ አዋጅ ቁ. 471/1998 እንደሆነ ይጠቅሳል፡፡ በአዋጁ አንቀጽ 14 የትምህር ሚኒስቴር የሚከተሉት ስልጣንና ተግባራት ተሰጥቶታል፡፡

  1. የትምህርት ስልጠና ስታንዳርድ ያወጣል፡፡ ሥራ ላይ መዋሉንም ያረጋግጣል፡፡
  2. የዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ 1 አጠቃላይ አነጋገር እንደተጠበቀ ሆኖ፣

ሀ) አጠቃላይ የስርዓተ ትምህርት ማእቀፍ ያዘጋጃል፡፡

ለ) ለአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ መምህራን አነስተኛውን የትምህርት ብቃት መለኪያ ያወጣል፡፡

ሐ) በሙያና ቴክኒክ ዘርፍ የሙያ ስልጠና ደረጃና የብቃት ማረጋገጫ ደረጃ ያወጣል፡፡

መ) የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሊያሟሉ የሚገባቸውን አነስተኛውን ደረጃ ያወጣል፡፡

  1. የከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ያቋቁማል፣ ያስፋፋል፤ ዕውቅና ይሰጣል፣ ጥራትና አግባብነት ያለው ትምህርት መስጠታቸውን ይቆጣጠራል፡፡
  2. ትምህርትና ስልጠናን በተመለከተ አገራዊ የአህዝቦት (በእንግሊዝኛው ቅጂ ‘popularization’) ተግባሮችን ያከናውናል፡፡

ከላይ የተዘረዘሩት ስልጣንና ተግባራት መመሪያውን ለማውጣት ስልጣን እንደሚያጎናጽፉ ድምዳሜ ከመያዙ በፊት አንድ መሰረታዊ ነጥብ መነሳት ይኖርበታል፡፡ ይኸውም፤ ማንኛውም መ/ቤት ከተቋምነቱ ወይም ከአጠቃላይ ስልጣንና ተግባራቱ የመነጨ መመሪያ የመደንገግ ስልጣን (inherent rulemaking power) የለውም፡፡ እያንዳንዱ ተቋም የስልጣኑ ምንጭ የተወካዮች ም/ቤት ውክልና እንደሆነ መቼም መዘንጋት የለበትም፡፡ የትምህርት ሚኒስቴር ሊጠቅስ የሚገባው ውክልና የሰጠውን የህግ ድንጋጌ ነበር፡፡ ስለሆነም ውክልና በሌለበት በትምህርት ተቋማት የአምልኮ ስርዓትን በሚመለከት መመሪያ መደንገግ ከስልጣን በላይ የሆነ ተግባር በመሆኑ መመሪያው የህጋዊነት መስፈርት አያሟላም፡፡

በተጨማሪም የአዋጅ ቁ. 471/1998 አንቀጽ 14 ድንጋጌ ይዘት የአምልኮ ስርዓት በትምህርት ሚኒስቴር እንዲወሰን አይፈቅድም፡፡ ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ መመሪያው በክልል መንግስታት ሊወሰን የሚገባውን ጉዳይ ጭምር አካቷል፡፡ በመመሪያው የትርጓሜ ክፍል የትምህርት ተቋማት የተባሉት ከመዋዕለ ህጻናት እስከ ዩኒቨርስቲ ድረስ ያሉትን በሙሉ ያጠቃልላል፡፡ የሕዝብ ትምህርት ቤቶችን አመራርና አስተዳደር፣ የትምህርት አሰጣጥ፣ የመምህራን አቀጣጠርና አስተዳደር በተመለከተ የትምህርት ሚኒስቴር ስልጣን የትምህርት ቤቶችን አመራርና አስተዳደር ለማጠናከር በወጣ (ማሻሻያ) አዋጅ ቁ. 217/1992 አንቀጽ 1 ተሽሮ ለብሔራዊ ክልላዊ መንግስታት እና የአዲስ አበባና ድሬዳዋ መስተዳድሮች ተላልፏል፡፡ በእነዚህ ትምህርት ቤቶች የአምልኮ ስርዓቱን በተመለከተ በህግ መወሰን/ያለመወሰን ስልጣኑም የእነዚህ አካላት ነው፡፡

 2. የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ሠራተኞች አስተዳዳር

ፍትህ የማግኘት መብትን የሚደነግገው የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ህገ መንግስት አንቀፅ 37/1/ እንደሚከተለው ይነበባል፡፡

ማንኛውም ሰው በፍርድ ሊወሰን የሚገባውን ጉዳይ ለፍርድ ቤት ወይም ለሌላ በህግ የዳኝነት ስልጣን ለተሰጠው አካል የማቅረብና ውሳኔ ወይም ፍርድ የማግኘት መብት አለው፡፡

የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ሰራተኞች አስተዳደር የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 155/2000 በልዩ ሁኔታ ሰራተኞችን ማሰናበትን በተመለከተ በአንቀጽ 37 እንደሚከተለው ደንግጓል፡፡

1) በዚህ ደንብ በሌላ ሁኔታ የተደነገገው ቢኖርም ዋና ዳይሬክተሩ በሙስና የተጠረጠረንና እምነት ያጣበትን ሰራተኛ መደበኛውን የዲስፕሊን አፈፃፀም ስርዓት ሳይከተል ከስራ ማሰናበት ይችላል

2) በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀፅ 1 መሰረት ከስራ የተሰናበተ ሰራተኛ በየትኛውም የፍርድ አካል ውሳኔ ወደ ስራ መመለስ አይችልም

የህገ መንግስቱና የደንብ ቁ. 155/2000 ድንጋጌዎች በስም (አንቀጽ ቁጥር) ይመሳሰላሉ፡፡ በተግባር ግን ተጻራሪ ናቸው፡፡ የመጀመሪያው መብት ያናጽፋል፤ ሁለተኛው ይነፍጋል፡፡ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ህገ መንግስቱን የማክበርና የማስከበር ግዴታ ከተጣለባቸው አካላት መካከል አንደኛው ነው፡፡ በዚህ ግዴታው የህግ አውጭነት ስልጣኑ ምንጭ የሆነው ህግ ያሰመረለትን ወሰን ሊያከብር ይገባል፡፡ ምክር ቤቱ ደንብ ቁ. 155/2000 ለማውጣት ህግ እንደፈቀደለት የሚጠቅሰው የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ለማቋቋም የወጣ አዋጅ አዋጅ ቁ. 587/2000 አንቀጽ 19/1/ ለ ድንጋጌ ነው፡፡ ይዘቱ እንደሚከተለው ይነበባል፡፡

[የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን] ሠራተኞች አስተዳደር የሚኒስትሮች ምክር ቤት በሚያወጣው ደንብ ይመራል፡፡

በስልጣን ምንጭነት የተጠቀሰው ህግ ም/ቤቱ በሠራተኞች አስተዳደር በተመለከተ ደንብ እንዲያወጣ ይፈቅድለታል፡፡ ይሁን እንጂ ሠራተኞች በጥርጣሬ እንዲሰናበቱና በየትኛውም የፍርድ አካል መብቸውን እንዳይጠይቁ የሚከለክል ኢ-ህገ መንግስታዊ ደንብ እንዲያወጣ ስልጣን አልሰጠውም፡፡

 3. የህብረህዋሳት ልገሳና ንቅለ ተከላ

የመድሀኒት፣ የምግብና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ደንብ ቁ. 299/2006 አንቀጽ 58-62 ድንጋጌዎች ስለ ደምና ደም ተዋጾ እና የሰውነት አካል ክፍሎችና የህብረህዋሳት ልገሳና ንቅለ ተከላ (donation of blood and blood products and donation and transplantation of organs and tissues) የሚከናወንባቸውን ሁኔታዎች ይደነግጋሉ፡፡ ደንቡ የወጣው የምግብ፣ የመድኃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር አዋጅ ቁ. 661/2002 አንቀጽ 55/1/ እና አሁን በአዋጅ ቁ. 916/2008[2] በተተካው አዋጅ ቁ. 691/2003[3] አንቀጽ 5 ለሚኒስትሮች ምክር ቤት በተሰጠ ስልጣን እንደሆነ በመግቢያው ላይ ተመልክቷል፡፡ አዋጅ ቁ. 661/2002 የአካላት ልገሳና ንቀለ ተከላ የሚመለከት ድንጋጌ አልያዘም፡፡ አንቀጽ 55/1/ ም/ቤቱ የሰጠው ስልጣን አዋጁን ለማስፈጸም የሚረዱ ደንቦች እንዲያወጣ ብቻ ነው፡፡ አዋጁ በዝምታ ያለፈውን ለዛውም ንቀለ ተከላን የሚያክል ትልቅ አገራዊ ጉዳይ በማስፈጸም ሰበብ በደንብ መወሰን የፓርላማን ቦታ መቀማት እንጂ በውክልና ህግ የማውጣት ተግባር (delegated legislation) አይደለም፡፡

እንደ ተጨማሪ የስልጣን ምንጭ የተጠቀሰው የአዋጅ ቁ. 691/2003 አንቀጽ 5 ትንሽ አግራሞት መፍጠሩ አይቀርም፡፡ ይዘቱ እንደሚከተለው ይነበባል፡፡

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሥልጣንና ተግባር በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 77 የተመለከተው ይሆናል፡፡

ህገ መንግስት ጠቅሶ ህግ ማውጣት የሚችለው የተወካዮች ምክር ቤት ብቻ ነው፡፡ በአንቀጽ 77 ንዑስ አንቀጽ 13 እንደሰፈረው የሚኒስትሮች ም/ቤት የተወካዮች ም/ቤት በሚሰጠው ስልጣን መሰረት ደንብ የማውጣት ስልጣን አለው፡፡ ስልጣን በማስተላለፍ የሚፈጠረው የወካይ-ተወካይ ግኝኑነት ሚኒስትሮችን ከአስፈጻሚነት በተጨማሪ የህግ አውጭነት ሚና ያላብሳቸዋል፡፡ ከዚህ በተቃራኒ በውክልና የተላለፈ ስልጣን በሌለበት የሚወጣ ማንኛውም ደንብ የህጋዊነትና ህገ መንግስታዊነት ገደቦችን ይጥሳል፡፡

ከላይ በምሳሌነት የተጠቀሱት አስተዳደራዊ ድንጋጌዎች አሳሳቢ እየሆነ የመጣውን የህጋዊነትና የህገ መንግስታዊነት ችግር ያንጸባርቃሉ፡፡ ውጤታማ የቁጥጥር ስልቶች ባልተረዘጉበት ሁኔታ በየጊዜው የሚወጡት መመሪያዎችና ደንቦች በስም ‘የበታች ህጎች’ በተግባር ግን ‘የበላይ ህጎች’ መሆናቸው አይቀርም፡፡

 4. የባንክ የዲሬክተሮች ቦርድ አባልነት

በሰ/መ/ቁ. 44226 (አመልካች የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እና ተጠሪዎች እነ ህብረት ኢንሹራንስ ኩባንያ /3 ሰዎች/ ታህሳስ 15 2003 .. ቅጽ 11) የአመልካች መመሪያ ከፊል ድንጋጌዎች ስልጣን የሰጠውን አዋጅ ስለሚቃረኑ ተፈጻሚነት እንዳይኖራቸው በተጠሪዎች ክስ ቀርቦ በፌደራል መጀመሪያ እና ከፍተኛ ፍርድ ቤቶች እንዲሻሩ ተወስኗል፡፡ ተቃውሞ የቀረበበት መመሪያ እ.ኤ.አ. 2006 ዓ.ም. የወጣው Directive No. SBB/39/2006 Licensing and Supervision of Banking Business፡ Amendment for New Bank Licensing and Approval of Directors and CEO ሲሆን የባንክ የዲሬክተሮች ቦርድ አባል በተመሳሳይ ጊዜ በሌላ የገንዘብ ተቋም የቦርድ አባል ሆኖ እንዳያገለግል፣ 75 ፐርሰንት አባላት የመጀመሪያ ዲግሪ እንዲኖራቸው እንዲሁም በድጋሚ መመረጥ እንዳይችሉ የተለያዩ ገደቦችን ይጥላል፡፡ ባንኩ መመሪያውን ያወጣው በጊዜው ጸንተው በነበሩት የገንዘብና ባንክ አዋጅ ቁ. 83/1986 አንቀጽ 41 እና የባንክ ስራ ፈቃድና ቁጥጥር አዋጅ ቁ. 84/1986 አንቀጽ 36 እንደሆነ በመመሪያ መግቢያ ላይ ተገልጿል፡፡

ጉዳዩ በሰበር ሲታይ ባንኩ መመሪያውን ለማውጣት ስልጣን እንዳለው በተደረሰበት ድምዳሜ መሰረት የስር ፍ/ቤቶች ውሳኔዎች ተሽረዋል፡፡ ሆኖም ለስልጣኑ ምንጭ ችሎቱ የጠቀሳቸው ድንጋጌዎች ባንኩ ራሱ በመመሪያው ላይ ካሰፈራቸው ይለያሉ፡፡ ችሎቱ ለህግ ትርጉሙ ድጋፍ ያደረገው የባንኩን የመቆጣጠር ስልጣን እና በሁለቱም አዋጆች በጥቅል የተነገው ባንኩ አዋጆቹን ለማስፈጸም የተሰጠው መመሪያ የማውጣት ስልጣን ነው፡፡

የማስፈጸም ዓለማ ያለው መመሪያ በሚያስፈጽመው አዋጅ ላይ ከተደነገጉ ጉዳዮች በላይ አልፎ ሊሄድ አይችልም፡፡ የመቆጣጠር ስልጣን እንዲሁ በህጉ ከተዘረጋው የቁጥጥር ማዕቀፍ ሊያፈነግጥ አይገባም፡፡ የመቆጣጠርና የማስፈጸም ስልጣን ብቻውን መመሪያውን ህጋዊ የሚያደርገው ከሆነ በባንኩ መመሪያ የማውጣት ስልጣን ላይ ምንም ዓይነት ገደብ ማስቀመጥ አይታሰብም፡፡ በዳይሬክተሮች ቦርድ አባልነት ላይ የሚደረጉ ገደቦችን በመመሪያ ለመወሰን መጀመሪያ ዋናው ህግ መሰረታዊ የፖሊሲ አቅጣጫዎችን ሊደነግግ ይገባል፡፡ የሰበር ችሎት ያንጸባረቀው አቋም ማናቸውንም የባንኩን መመሪያዎች ህጋዊነት ያለጥያቄ አስቀድሞ የማጽደቅ ያክል ነው፡፡

[1] በትምህርት ተቋማት የአምልኮ ስርዓትን በሚመለከት የወጣ መመሪያ፡ የትምህርት ሚኒስቴር ህዳር 2000 ዓ.ም.

[2] የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ ስራ አስፈጻሚ አካላትን ስልጣንና ተግባር መወሰኛ አዋጅ ቁ. 916/2008

[3] የኢትዮዽያ ፌደራላዊ ዲሞከራሲያዊ ሪፐብሊክ አስፈፃሚ አካላትን ስልጣንና ተግባር ለመወሰን የወጣ አዋጅ ቁ. 691/2003


Filed under: Articles, Constitution and Human rights, Constitutional law, Directives, Education law, National Bank of Ethiopia

Viewing all articles
Browse latest Browse all 992

Trending Articles



<script src="https://jsc.adskeeper.com/r/s/rssing.com.1596347.js" async> </script>