Quantcast
Channel: Ethiopian Legal Brief
Viewing all articles
Browse latest Browse all 992

የህዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም በክልሎች ላይ ያለው ስልጣን ህገ-መንግስታዊ ስላለመሆኑ –ክፍል ፩

$
0
0

በህዝብ እንባ ጠባቂ ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 211/1992 አንቀጽ 4 መሰረት በፌደራሉ መንግስት የተቋቋመው ፌደራል እንባ ጠባቂ በክልል መንግስት ስራ አስፈጻሚ አካላትና ባለስልጣናት የሚፈፀሙ የአስተዳደር ጥፋቶችን የመመርመር ስልጣን ተሰጥቶታል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ ቁ. 210/1992 አንቀጽ 4 አዋጁ በማንኛውም ክልል ውስጥ በሚፈፀሙ የሰብዓዊ መጣስ ጉዳዮችም ላይ ስልጣን እንደሚኖረው ይደነግጋል፡፡ የሁለቱም አዋጆች አንቀጽ 4 አፈላጊነት ሆነ ህገ-መንግስታዊነቱ በሚገባ የተመከረበትና የታሰበበት ካለመሆኑም በላይ በተግባር የክልሎችን የዲሞክራሲያዊ ተቋም ግንባታ ጅምሮ ከማዳከም በቀር ተጨባጭ ፍሬ አላስገኘም፡፡

የዚህ ጽሁፍ ዋና ዓላማ ተቋሙ ሆኖ ኮሚሽኑ በክልሎች ላይ የተሰጣቸው ስልጣን የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ህገ-መንግስት የማይፈቅደው ስለሆነም ህገ-መንግስታዊ መሰረት እንደሌለው ብሎም ከተግባራዊ ምክንያቶች አንጻር የማያስኬድና ለአፈፃፀም የማይመች ስለመሆኑ አሳማኝ መከራከሪያዎች ማቅረብ ነው፡፡

ቀጥሎ በሚቀርው ዳሰሳ ውስጥ በተለየ ሁኔታ ካልተመለከተ በስተቀር እንባ ጠባቂ የሚለው ቃል በተመሳሳይ መልኩ ኮሚሽኑንም ያጠቃልላል፡፡ በሁለቱም ማቋቋሚያ አዋጆች ላይ የሚገኙት ድንጋጌዎች ከይዘት አንጻር ብቻ ሳይሆን ከአንቀጽ አቀማመጥ ጀምሮ ተመሳሳይነት አላቸው፡፡ በተጨማሪም ኮሚሽኑ ሆነ ተቋሙ ስያሜያቸው ቢለያይም በአሰራርም በተግባርም በስልጣንም /Power/ ሁለቱም ያው እንባ ጠባቂዎች ናቸው፡፡ በሁለቱ መካከል ያለው ቀጭን ልዩነት የስልጣን ክልል (jurisdiction) ልዩነት ነው፡፡ የህዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም የአስተዳደር ጥፋቶችን ኮሚሽኑ ደግሞ የሰብዓዊ መብት መጣስ ጉዳዮችን በተመለከተ የመመርመር የመከታተል፣ የመቆጣጠርና የመመርመር ስልጣን አላቸው፡፡ በሌላ አነጋገር ኮሚሽኑ የሰብዓዊ መብት ጉዳዮች እንባ ጠባቂ ሲሆን ተቋሙ ደግሞ የአስተዳደር ጥፋቶች እንባ ጠባቂ ተብሎ ሊፈረጅ ይችላል፡፡ በዚህ የተነሳ ከዚህ በታች የሚቀርቡት መከራከሪያዎች ላይ በጥቅሱ እንባ ጠባቂ የሚለው ቃል ለሁለቱም በወካይነት ጥቅም ላይ ውሏል፡፡ በመከራከሪየነት የሚነሱት መሰረታዊ ነጥቦች የሚከተሉት ናቸው፡፡

  • እንባ ጠባቂ የማቋቋም ህገ-መንግስታዊ ግዴታ
  • ራስን በራስ የማስተዳደር መብት
  • እንባ ጠባቂ-እንደ ፓርላማ ክንፍ
  • የተቋሙ መፍትሔ ይዘትና አፈጻጸም
  • የአቅም ውስንነት
  • ለተቋሙና ተሿሚው ያለው ከበሬታ

እንባ ጠባቂ የማቋቋም ህገመንግስታዊ ግዴታ

እንባ ጠባቂ በክልል መንግስታት ላይ ስልጣን ሊኖረው ይገባል ወይስ አይገባም? የሚለው ጥያቄ ተቋሙን ሆነ ኮሚሽኑን በኢትዮጵያ ውስጥ በዝርዝር ህግ ለማቋቋም ከታሰበበት ጊዜ አንስቶ እስከ አሁን ድረስ ገሃድ የወጣ ክርክርና ውይይት አልጋበዘም፡፡ በክልል መንግስታት ዘንድም ውስጥ ውስጡን የጉርምርምታ ምንጭ ቢሆንም ጉዳዩ በጭብጥነት ተመዞ የመነጋገሪያ አጀንዳ ለመሆን አልበቃም፡፡ ተቋሙንና ኮሚሽኑን ለማቋቋም በነበረው የህግ ማውጣት ሂደት እንደዚሁ ሁለቱም አካላት በክልሎች ላይ የሚኖራቸው ስልጣን ህገ-መንግስታዊነትና ተግባራዊነት በተመለከተ ህገ-መንግስቱን ተንተርሶ የተሰጠ ትንተና ሆነ ምክንያት አልነበረም፡፡

ከላይ እንደተጠቆመው የሁለቱም ተቋማት ማቋቋሚያ አዋጆች በክልል መንግስት ስራ አስፈጻሚ አካላትና ባለስልጣናት የሚፈፀሙ የአስተዳደር ጥፋቶችና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች በተቋሙና በኮሚሽኑ የስልጣን ክልል ስር እንደሚወድቁ ደንግገዋል፡፡   በዚህ ረገድ የተፈጠረው የተሳሳተ ግንዛቤ ምንጩ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ህገ መንግስት አንቀፅ 55 ንኡስ አንቀፅ 14 እና 15 ንባብ ስለመሆኑ አያጠራጥርም፡፡ ሁለቱም አንቀጾች የተወካዮች ምክር ቤት ስልጣንና ተግባር በሚዘረዝረው የህገ መንግስቱ አንቀፅ 55 ውስጥ የሚገኙ ሲሆን ምክር ቤቱ የሠብዓዊ መብት ኮሚሽንንና የእንባ ጠባቂ ተቋምን እንደሚያቋቁም ብሎም ስልጣንና ተግባራቸውን በህግ እንደሚወሰን በማያሻማ አነጋገር ይደነገጋሉ፡፡

የአንቀጽ 55/14/ እና /15/ ድንጋጌዎችን ላይ ላዩን ለሚያነብ ሰው ሁለቱም ተቋማት በፌደራል መንግስት ስልጣን ስር እንደሚካተቱ የተሳሳተ ድምዳሜ ላይ ሊደርስ ይችላል፡፡ የሁለቱም ተቋም ማቋቋሚያ አዋጆች በሚረቀቁበት ወቅት ተቋማቱን አስመልክቶ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በቀረበ አንድ ሪፖርት ላይ ተቋማቱ በክልሎች ላይ ስልጣን ሊኖራቸው እንደሚገባ ለማሳመን የህገ-መንግስቱ አንቀፅ 55 /14/እና /15/ ተጠቅሰዋል፡፡ ስለሆነም በዚህ ረገድ ያለውን የተሳሳተ ግንዛቤ ማጥራት ያስፈልጋል፡፡

የእንባ ጠባቂ በየአገራቱ ዝብርቅርቅ መልክና ቅርጽ አለው፡፡ ሆኖም ከሚቋቋምበት መንገድ አንጻር ሲታይ በአንድ መንግስታዊ ተቋም ስር (ለምሳሌ የዩኒቨርስቲ[1] እና የማረሚያ ቤት እንባጠባቂ[2])፣ በግሉ ዘርፍ (ለምሳሌ የባንኮች፣ የኃይል አቅርቦት፣ የኢንሹራንስ፣ የቴሌኮሙኒኬሽን እንባጠባቂዎች[3]) እንዲሁም በጣም በሚታወቅበት መልኩ በአገር አቀፍ፣ በክልሎች፣ ግዛቶችና መስተዳድሮች ደረጃ ይቋቋማል፡፡

በግሉ ዘርፍ እና በተቋም ደረጃ የሚገኘውን ትተን በአገር ዓቀፍ ደረጃ የሚቋቋመውን እንባ ጠባቂ በጥቅል ስንመለከት የሚቋቋምበት መንገድ ሁለት ነው፡፡ ይኸውም አንደኛ አገሪቱ ባጸደቀችው ህገ መንግስት በግልጽ ዕውቅና የተሰጠው ሊሆን ይችላል፡፡ ሁለተኛ በህገ መንግስት ላይ በግልጽ ሳይካተት ፓርላማ በሚያወጣው ልዩ ህግ ሊቋቋም ይችላል፡፡ የተቋሙ የህልውና መሰረት ህገ መንግስት መሆኑ/አለመሆኑ አንድ መሰረታዊ ቁምነ ነገር ያስጨብጠናል፡፡ ይኸውም ህገ መንግስታዊ ዕውቅና ያለው እንባ ጠባቂ ተቋም የመቋቋሙ ዕጣ ፈንታ ለህግ አውጪው የተተወ አይደለም፡፡ ህግ አውጪው መዋቅርና አደረጃጀቱን በልዩ ህግ በመወሰን ተቋሙን የመመስረት ህጋዊ ግዴታ አለበት፡፡ በተቃራኒው የአንድ አገር ህገ መንግስት ስለተቋሙ በግልጽ ካልደነገገ እንደ ህግ አውጪው ፈቃድ እንባ ጠባቂ ሊኖርም ላይኖርም ይችላል፡፡ ህልውና የሚያገኘው አስፈላጊነቱና ጠቃሚነቱ ከታመነበት ብቻ ነው፡፡

የእንባ ጠባቂ ጽንሰ ሀሳብ በአጭር ጊዜ ውስጥ ፈጣን ዕድገት በማሳየት ከሞላ ጎደል በሁሉም የዓለማችንን አገራት ሰፊ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ ተቋሙ የመንግስትን ተጠያቂነት በማረጋገጥ ብሎም አስተዳደራዊ ፍትሕ በማስፈን ሊጫወት የሚችለው ዴሞክራሲያዊና ህገ መንግስታዊ ሚና መሰረታዊ ጥያቄ ባይነሳበትም የተወሰኑ አገራት እጃቸውን ዘርግተው አልተቀበሉትም፡፡ ሌሎች ደግሞ ትልቅ ቦታ ከመስጠታቸው የተነሳ ህልውናው በየምርጫ ዘመን በሚቀያየር ፓርላማ ላይ ጥገኛ እንዳይሆን በማሰብ ጠንካራ ህገ መንግስታዊ መሰረት እንዲኖረው አድርገውታል፡፡ የተቀሩት ደግሞ ህገ መንግታዊ ዕውቅና እስከ መስጠት ደረጃ ባይደርሱም በልዩ ህግ በማቋቋም ህልውና እና ዕውቅና ሰጥተውታል፡፡ ስለሆነም ሲፈለግ ይኖራል፤ ከገዜ በኋላ ካልተፈለገ ይቀራል፡፡

አልባኒያ the People’s Advocate በመባል የሚጠራውን እንባ ጠባቂ ተቋም እ.ኤ.አ በ1998 ዓ.ም. ባጸደቀችው ህገ መንግስት ላይ የማቋቋሚያውን መሰረት ከጣለች በኋላ በቀጣዩ ዓመት በይፋ ህግ እንዲቋቋም አድርጋለች፡፡[4] ሆኖም የኦስትሪያ እንባ ጠባቂ ቦርድ ህገ መንግስታዊ መሰረት ስላልነበረው ተቋሙን የማቋቋም ሀሳብ መጀመሪያ ተቀባይነት ሳያገኝ ከጊዜ በኋላ በህግ ሊቋቋም ችሏል፡፡ የህጉ ረቂቅ ለፓርላማ የቀረበው እ.ኤ.አ በ1972 ዓ.ም. ሲሆን ከሶስት ዓመታት በኋላ ተቀባይነት ሳያገኝ በመቅረቱ ውድቅ ተደርጓል፡፡ ሆኖም ከዚሁ ረቀቂ ይዘትና መንፈስ በመነሳት በድጋሚ የቀረበው ረቂቅ እ.ኤ.አ በ1977 ተቀባይነት አግኝቶ ቦርዱ ሊቋቋም ችሏል፡፡[5] በአሜሪካ የፌደራል እንባ ጠባቂ የሚባል ተቋም የለም፡፡ ኮንግረስ ስራ አስፈጻሚውን መቆጣጠር ለራሱ ብቻ የተተወ ህገ መንግስታዊ ሚና እንደሆነ ጠንካራ አቋም በመያዙ ይህን ታሪካዊ ስልጣኑን አሳልፎ መስጠት አልፈቀደም፡፡[6] የዚህ አመለካከት ተጽዕኖ ተቋሙ ከጥቂት ግዛቶች[7] በስተቀር በአብዛኞቹ ተቀባይነት እንዳያገኝ ምክንያት ሆኗል፡፡

ወደ አገራችን ስንመጣ ሁለቱም ተቋማት በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 55/14/ እና /15/ ላይ መሰረታቸው ተጥሏል፡፡ የተወካዮች ምክር ቤት ስልጣንና ተግባራቸውን በዝርዝር ህግ ከመወሰን ውጪ አስፈላጊነታቸውን ጥያቄ የሚያነሳበት ጉዳይ አይደለም፡፡ ሁለቱም ድንጋጌዎች በግልጽ የሚናገሩት ምክር ቤቱ ተቋማቱ ህጋዊ ሰውነት አግኝተው ስራቸውን እንዲያከናውኑ የማድረግ ህገ መንግስታዊ ግዴታ እንዳለበት ነው፡፡ ይሄ ግዴታ በሌሎች ሶስት ህግ መንግስታዊ መሰረት ባላቸው ተቋማትም ላይ ተፈጻሚነት አለው፡፡ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ህገ መንግስት ከአንቀጽ 111-113 ድረስ የተጠቀሱት የዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት፣ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ እና የህዝብ ቆጠራ ኮሚሽን እንደ እንባ ጠባቂ ሁሉ ህገ መንግስታዊ ናቸው፡፡

የድንጋጌዎቹን ይዘት ከፌደራላዊ የስልጣን ክፍፍል ጋር ማምታታት የፌደራላዚም ስርዓት ሀሁ ግንዛቤ የማጣት ያክል ነው፡፡ የአንቀጽ 55 ርዕስ ‘ስልጣንና ተግባር’ ስለሚል ብቻ ሁለቱም ተቋማት በፌደራል መንግስት የስልጣን ክልል ስር እንደሆኑ ማሰብ ትርጉም አለመስጠቱ ብቻ ሳይሆን ፌደራሊዝምን በአሀዳዊነት መነጽር የማየት ችግር ያንጸባርቃል፡፡

ለመሆኑ ‘እንባ ጠባቂ ተቋም እና የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በፌደራል መንግስት ስልጣን ስር ናቸው ማለት ምን ማለት ነው?’ በፌደራል እና ክልል ስልጣን (jurisdiction)[8] ስር የሚወድቁ ጉዳዮች በአንቀጽ 51 እና 52 ስር ተለይተው ተዘርዝረዋል፡፡ ዝርዝሮቹ በሙሉ የሚናገሩት በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ዘርፍ ስር ስላሉ ጉዳዮች ነው፡፡ ስልጣን በፌደራል እና በክልል የሚከፋፈለው አንድ ተቋም በሚያከናውነው ጉዳይ እንጂ ተቋሙን ራሱን የፌደራል/የክልል በማለት አይደለም፡፡ ለዚህም ነው እንባ ጠባቂ የፌደራል ብቻ ነው የሚል አነጋገር ትርጉም የማይሰጠው፡፡

ህገ መንግስቱ የክልል መንግስታት የራሳቸውን እንባ ጠባቂና ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን እንደሚያቋቁሙ ሳይናገር በዝምታ ማለፉ ተገቢና ትክክል ነው፡፡ ምክንያቱም ውሳኔው ከመነሻው የክልሎቹ የራሳቸው ነው መሆን ያለበት፡፡ ሲፈልጉ በህገ መንግስታቸው ለተቋማቱ ዕውቅና መስጠት ይችላሉ፡፡ አሊያም ደግሞ በህገ መንግስታቸው ውስጥ ማካተቱን ትተው አስፈላጊ ሆኖ ባገኙት ጊዜ ህግ አውጥተው ማቋቋም (አሊያም እስከነጭራሹ አለማቋቋም) ይችላሉ፡፡

ሲጠቃለል የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 55 /14/ እና /15/ ድንጋጌዎች ይዘት የፌደራሉ እንባ ጠባቂ ህገ መንግስታዊ እንደሆነና የተወካዮች ምክር ቤት በዝርዝር ህግ ስልጣንና ተግባሩን በመወሰን ህጋዊ ሰውነት ኖሮት እንዲቋቋም የማድረግ ህገ መንግስታዊ ግዴታ እንዳለበት ነው፡፡ ስለሆነም ሁለቱም ተቋማት በክልል መንግስታት ስራ አስፈጻሚ ላይ ስልጣን እንዳላቸው ከድንጋጌዎቹ በመነሳት የሚቀርብ ክርክር ፈር የሳተና የፌደራል ስርዓት ከሚያስነሳቸው ዘርፈ ብዙ ጭብጦች ውስጥ ሊካተት የማይችል፣ ጥልቀት ያነሰው፣ ‘ከላይ-በላይ ንባብ’ የሚመነጭ ክርክር ነው፡፡ ብዙ ባያስኬድም ከስልጣን ክፍፍል አንጻር ክርክር ከቀረበ መቅረብ ያለበት ተቋማቱ ከፌደራልና ከክልል በየትኛው ስልጣን ስር እንደሚወድቁ በመጠየቅ ሳይሆን ተቋማቱ የሚያከናውኑት ጉዳይ በማን ስልጣን ስር እንደሆነ ጥያቄ በማንሳት ነው፡፡ ስለሆነም ጥያቄው የሚከተለውን መልክ ይይዛል፡፡ ‘የክልል ስራ አስፈጻሚ አካላትንና ባለስልጣናትን ተጠያቂነት ማረጋገጥ፣ በክልሉ አስተዳደራዊ ፍትሕ ማስፈን፣ ለአስተዳደራዊ በደሎች መፍትሔ መስጠት፣ አስተዳደራዊ ጥፋትን የማረም ስልጣኑ የማን ነው? የራሱ የክልሉ ነው? ወይስ የፌደራል መንግስት? በክልል ጉዳይ የሚያገባው ማነው? የፌደራል ወይስ የክልሉ መንግስት?’

የጥያቄዎቹ ቀላልነት ሲታይ ምላሽ መስጠት መሰረታዊ ባልሆነ ጉዳይ መባከን ተደርጎ ሊቆጠር ይችላል፡፡ ይሁን እንጂ ከ500 በላይ አባላት ያቀፈ ፓርላማ ጥያቄውን በወጉ መመለስ ተስኖት ‘ፈተናውን የወደቀ’ እንደመሆኑ በቂ ማብራሪያ መስጠት ግድ ይላል፡፡

[1] ለበለጠ ግንዛቤ Mundinger, Donald C. 1967. “The University Ombudsman: His Place on the Campus.” The Journal of Higher Education (Ohio State University Press) 493-499. Accessed June 27, 2014. http://www.jstor.org/stable/1980338. ይመለከቷል፡፡

[2] ለበለጠ ግንዛቤ Fulmer, Richard H. 1981. “The Prison Ombudsman.” Social Service Review (The University of Chicago Press) 55: 300-313. Accessed June 27, 2014. http://www.jstor.org/stable/30011474. ይመለከቷል፡፡

[3] Trevor Buck, Richard Kirkham and Brian Thompson, The Ombudsman enterprise and administrative Justice. (ashgate publishing company፣ 2011) ገፅ 7

[4] Joachim Stern, Albania. In G. Kucsko-Stadlmayer (Ed.), European Ombudsman-Institutions A comparative legal analysis regarding the multifaceted realisation of an idea. (SpringerWienNewYork, 2008) ገፅ 70

[5] Brigitte Kofler, Austria. In G. Kucsko-Stadlmayer (Ed.), European Ombudsman-Institutions A comparative legal analysis regarding the multifaceted realisation of an idea. (SpringerWienNewYork, 2008) ገፅ 90

[6] Kass, Benny L. 1967. “We Can, Indeed, Fight City Hall: The Office and Concept of Ombudsman.” American Bar Association Journal (American Bar Association) 53 (3): 231-236. Accessed June 28, 2104. http://www.jstor.org/stable/25723944.

[7] ለምሳሌ ሀዋይ፣ ኔብራስካ፣ አዮዋ፣ አላስካና አሪዞና የእንባ ጠባቂ ተቋም በህግ አቋቁመዋል፡፡ Hill, Larry B. 2002. “The Ombudsman Revisited: Thirty Years of Hawaiian Experience.” Public Administration Review (Wiley/American Society for Public Administration) 61: 24-41. Accessed June 27, 2014. http://www.jstor.org/stable/3110280.

[8] ምንም እንኳን በኢ.ፌ.ዲሪ. ህገ መንግስት አንቀጽ 51 እና 52 የእንግሊዝኛ ቅጂ ርዕሶች ላይ ህግ አውጪው የተጠቀመው powers and duties የሚል ቢሆንም የስልጣን ክልልን ወይም ወሰንን በአግባቡ የሚገልጸው ቃል jurisdiction ነው፡፡


Filed under: Articles

Viewing all articles
Browse latest Browse all 992

Trending Articles



<script src="https://jsc.adskeeper.com/r/s/rssing.com.1596347.js" async> </script>