Quantcast
Channel: Ethiopian Legal Brief
Viewing all 992 articles
Browse latest View live

ይርጋ፡ ማንሳት መተው መቋረጥ እና መነሻ ጊዜ

$
0
0

ይርጋ

በህግ ተለይቶ ከተቀመጠው የጊዜ ገደብ በኋላ በአንድ ጉዳይ ክስ ለማቅረብ የሚከለከልበት የህግ ፅንሰ-ሃሳብ

ይርጋ አንድ ሰው በጉዳዩ ላይ መብት ያለው ቢሆንም እንኳን ይህንን መብቱን ለመጠየቅ የማይችልበትን ገደብ የሚመለከት ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 44800 ቅጽ 10[1]

የይርጋ ህግ መሰረታዊ አላማ ተገቢውን ጥረት የሚያደርጉ ገንዘብ ጠያቂዎችን ወይም መብት አስከባሪዎችን መቅጣት ሳይሆን መብታቸውን በተገቢው ጊዜ ለመጠየቅ ጥረት የማያደርጉትን ሰዎች መቅጣት መሆኑ ይታመናል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 98358 ቅጽ 17[2]

የይርጋ መቃወሚያ ማንሳት

ክሱ በይርጋ ቀሪ እንደሚሆን በመግለጽ የመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያ /በተከሳሽ/ ማቅረብ

የይርጋ ደንብ ተፈጻሚ የሚሆነው ክስ ከቀረበ በኋላ ተከሳሹ የይርጋ መቃወሚያ አንስቶ የተከራከረ ከሆነ ነው፡፡ ከሳሽ ክስ የማቅረብ መብቱ በይርጋ ቀሪ ከሆነ በኋላ ክስ አቅርቦ ተከሳሽ ክሱ በይርጋ ቀሪ መሆኑን በመግለጽ ካልተቃወመ ክሱ ተቀባይነት አግኝቶ መታየት ይቀጥላል፡፡ የጊዜ ገደቡ በማለፉ ብቻ ፍ/ቤት ይርጋውን በራሱ አነሳሽነት አንስቶ ክሱን ውድቅ ሊያደርግ አይችልም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 44800 ቅጽ 10[3]

በመርህ ደረጃ የይርጋ ጥያቄ በተከራካሪዎች ካልተነሳ ፍርድ ቤቱ በራሱ አነሳሽነት ሊያነሳው አይችልም፡፡ የይርጋን ጉዳይ የማንሳት ወይም ያለማንሳት ኃላፊነት ሙሉ በሙሉ የተከሳሽ ወገን ነው፡፡ ይህ አጠቃላይ መሰረተ ሀሳብ ግን ባልተነጣጠለ ኃላፊነት በተከሰሱ ተከሳሾች ላይ ተፈጻሚነት የለውም፡፡ በዚህን ጊዜ በአንደኛው ተከሳሽ የሚነሳ የይርጋ መቃወሚያ ክሱን በይርጋ ቀሪ የሚያደርገው ቢሆን መቃወሚያው በሁሉም ተከሳሾች እንደተነሳ ተቆጥሮ ክሱ ውድቅ መደረግ ይኖርበታል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 19081 ቅጽ 4፣[4] ፍ/ህ/ቁ. 1677፣ 1901

ተከራካሪዎች የይርጋ ጥያቄ እስካቀረቡ ድረስ ጥያቄውን በትክክለኛው አንቀጽ መሰረት እንዲመራ ማድረጉ የፍርድ ቤት ሃላፊነት ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 17937 ቅጽ 4፣[5] ፍ/ህ/ቁ. 1000፣ 1677፣ 1845

የይርጋ ደንብ አንድ ክስ በፍርድ ቤት ቀርቦ በስረነገር እንዳይታይ የሚከለክል ሲሆን የሕሊና ግምት (በ2024 የሰፈረው የመክፈል ግምትን ጨምሮ) በሌላ በኩል የማስረዳት ሸክምን ከአንድ ወገን ወደ ሌላው የማስተላለፍ ውጤት ብቻ ያለው በመሆኑ ከሣሽ ያቀረበውን ክስ ይዘት መርምሮ ውሣኔ መስጠትን የሚከለክል አይደለም፡፡ በፍትሐብሔር ሕጉ ውስጥ የሰፈረውን ይርጋ ተከሣሹ ወገን ካላነሳው ፍርድ ቤቱ በራሱ ሊያነሳ እንደማይችል በፍትሐብሔር ሕግ ቁ.1856 የተጠቀሰ ቢሆንም ይህ ድንጋጌ ተፈጻሚነት የሚኖረው ለይርጋ ድንጋጌዎች እንጂ በሕግ ግምት የማስረዳት ሸክም ከአንድ ተሟጋች ወደ ሌላው በሚዘዋወርባቸው ሁኔታዎች አይደለም፡፡

በመሆኑም ይርጋን (Period of limitation) ከሕግ ግምት (Presumptions) ጋር በማመሳሰል ለይርጋ ተፈፃሚ የሚሆነው ሕግ ለህግ ግምትም ተፈፃሚ መሆን ይገባዋል በማለት የሚቀርብ ክርክር የህጉን መንፈስ፣ ዓላማና ግልጽ ይዘት ያልተከተለ በመሆኑ ተቀባይነት የለውም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 17068 ቅጽ 1[6]

ይርጋ መተው

አንድ ሰው የይርጋ ጊዜውን ትቶታል የሚባለው ለዕዳው ምንጭ የሆነውን ግዴታ በማመን አዲስ መተማመኛ ሰነድ የሰጠ እንደሆነ ነው፡፡ ይርጋን መተው ውጤቱ ይርጋን የሚያቋርጥ ሳይሆን አዲስ የይርጋ ጊዜ መቆጠር እንዲጀምር ያደርጋል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 90361 ቅጽ 6[7]

ይርጋ መቋረጥ

በፍ/ብ/ሕ/ቁ/1852 ድንጋጌ መሠረት ይርጋ በተቋረጠ ጊዜ ከተቋረጠበት ጊዜ ጀምሮ እንደገና አዲስ የይርጋ ዘመን መቁጠር እንደሚጀምር በዚሁ ድንጋጌ በንዑስ ቁጥር /1/ ሥር ተመልክቷል፡፡ ከዚህ ድንጋጌ በግልጽ መረዳት የሚቻለው ይርጋው በተቋረጠ ጊዜ ቀድሞ የነበረው የይርጋ ጊዜ እንደ አዲስ መቁጠር የሚጀምር መሆኑን ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 31185 ቅጽ 6[8]

በሕግ ተለይቶ የተወሰነ የይርጋ ጊዜ የመቋረጥ እና ያለመቋረጥ ጉዳይ አከራካሪ ነጥብ ሆኖ ሊነሳ የሚችለው የይርጋውን መቆጠር ያቋርጠዋል የተባለው ምክንያት የተከሰተው የይርጋው ጊዜ ከመሙላቱ በፊት በሆነ ጊዜ እንጂ የይርጋው ጊዜ የሞላ ወይም ያለፈ በሆነ ጊዜ ጭምር አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 90361 ቅጽ 6[9]

ክስ የማቅረብ ውጤት

ስልጣን ለሌለው የዳኝነት አካል ክስ ማቅረብ ይርጋን ያቋርጣል፡፡

(በመዝገብ ቁጥር 16648 ስለ ይርጋ ጊዜ አቆጣጠርና ስለ ይርጋ መቋረጥ የተሰጠው የሕግ ትርጉም ተለውጧል፡፡)

ሰ/መ/ቁ. 36730 ቅጽ 9[10]

ክስ የማቅረብ ውጤት /ሽያጭ ውል/

ይርጋ ከሚቋረጥባቸው ምክንያቶች አንደኛው ባለገንዘቡ መብቱ እንዲታወቅለት በፍ/ቤት ክስ አቅርቦ ለባለእዳው አስታውቆ የተገኘ እንደሆነ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 43992 ቅጽ 10፣[11] ፍ/ህ/ቁ. 1851(ለ)

ክሱ የቀረበው መብቱን በሚጠይቀው ባለገንዘብ ባይሆንም ባለዕዳው በባለገንዘቡ ላይ ያቀረበው ክስ በይዘቱ የይርጋ መቃወሚያ ከተነሳበት ክስ ጋር ተያያዥነት ካለው ይርጋውን ያቋርጠዋል፡፡

የማይንቀሳቀስ ንብረት ገዢ ንብረቱን ለመረከብ (የሽያጭ ውሉ እንዲፈጸምለት) ያቀረበው ክስ ከሽያጭ ውሉ ቀን ጀምሮ ሲቆጠር በይርጋ የሚቋረጥ ቢሆንም ሻጭ ቀደም ብሎ የሽያጭ ውሉ እንዲፈርስለት ክስ ካቀረበ በገዢው ላይ ተፈጻሚ የሚሆነውን የይርጋ ጊዜ ያቋርጠዋል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 43636 ቅጽ 10[12]

በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1776 እና በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 1 እና 2 ድንጋጌዎች መሠረት የቤት ሽያጭ ውል ይፈጸምልኝ ክስ ሲቀርብ በሕግ የተደነገገው የይርጋ ሕግ የጊዜ ገደብ አልፏል ወይስ አላለፈም? የሚለውን ነጥብ ለመወሰን በመጀመሪያ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 ድንጋጌ ይዘት መንፈስና ዓላማ እንደዚሁም ድንጋጌው ከፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2875 መሠረታዊ መርህና ስለ ሽያጭ እና ጠቅላላ ውል ከተደነገጉ ድንጋጌዎች ጋር ሊኖረው የሚገባውን ተፈፃሚነት መመርመር ያስፈልጋል፡፡

  1. የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2893 ንዑስ አንቀጽ 3 “ስለሆነም ሻጭ ውሉን እንደውሉ ቃል ለመፈፀም መዘግየቱን ከተረዳበት ጊዜ አንስቶ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ውሉ እንዲፈፀምለት ካልጠየቀ በቀር ገዢው ውሉ በግዴታ እንዲፈፀም የማድረግ መብቱን ያጣል” በማለት ይደነግጋል፡፡ እዚህ ላይ በአማርኛው “መዘግየቱን ከተረዳበት” በሚለውና በእንግሊዘኛው “ascertained” በሚለው ቃል መካከል ልዩነት ያለመሆኑን ለመገንዘብ እንችላለን፡፡ የድንጋጌው መንፈስ ገዥ በአንድ ዓመት ውስጥ ውሉ እንዲፈፀምለት ለፍርድ ቤት ክስ ማቅረብ ያለበት ሻጭ በሽያጭ ውሉ መሠረት ለመፈፀም ፈቃደኛ አለመሆኑን ካረጋገጠበት ጊዜ ጀምሮ እንደሆነ የእንግሊዘኛውን የቃል አጠቃቀም በማየት ለመረዳት ይቻላል፡፡

እዚህ ላይ የሚነሣው ጥያቄ ሻጭ በሽያጭ ውሉ መሠረት ለመፈፀም እንደማይፈልግ ገዥ ያረጋገጠ መሆኑን የማስረዳት ግዴታ ያለበት ማን ነው? የሚለው ነው፡፡ ለዚህ መሠረታዊ ነጥብ እልባት ለመስጠት ስለውል እና ተዋዋይ ወገኖች በፍትሐብሔር ሕጉ የተቀመጠ የሕግ ግምቶችን ማየት አስፈላጊ ነው፡፡

  1. በሕግ አግባብ የተቋቋሙ ውሎች ባቋቋሟቸው ሰዎች ላይ ሕግ ናቸው በማለት የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1731ንዑስ አንቀጽ 1 የደነገገ ሲሆን ውሎች በተዋዋይ ወገኖች መካከል ሊኖር የሚገባውን የቅንነት የመተማመን ግንኙነት መሠረት በማድረግ በቅን ልቦና ሊተረጎሙ እንደሚገባ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1732 ይደነግጋል፡፡ ከዚህ አንፃር ስናየው ተዋዋይ ወገኖች በተዋዋሉት የውል ቃል መሠት ውሉን የመፈፀም ፍላጎትና ቅን ልቦና ያላቸው መሆኑ የውል ሕግ ግምት የሚወስድበት ጉዳይ በመሆኑ ገዥ ሻጭ በሽያጭ ውሉ በገባው የውል ቃል መሠረት እንደሚፈጽም የተለያዩ የተስፋ ቃሎችን ሲሰጠው የቆየ መሆኑን የማስረዳት ግዴታ የለበትም፡፡

በተቃራኒው የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 ድንጋጌን ጠቅሶ የሚከራከር ሻጭ ከገዥ ጋር ባደረገው የቤት ሽያጭ ውል መሠረት ለመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን ገዥ በማያሻማ ሁኔታ እንዲያውቅ እና እንዲረዳው ያደረገ መሆኑን የማስረዳት ግዴታ አለበት፡፡ ሻጭ በውሉ መሠረት ለመፈፀም እንደማይፈልግ በእርግጠኝነት ገዥ እንዲያውቅ ካደረገው ከአንድ ዓመት በኋላ የሽያጭ ውሉ በፍርድ ኃይል እንዲፈፀምለት የጠየቀ መሆኑን የማስረዳት ግዴታ አለበት፡፡ ስለሆነም የማይንቀሣቀስ ንብረት የሸጠ ሰው ሻጭ በሽያጭ ውሉ መሠረት የቤቱን ይዞታና የባለቤትነት ሰነዶች ለገዥ ያላስረከበ ከሆነ ውሉን ለመፈፀም ፈቃደኛ አለመሆኑንና በጽሑፍና በማያሻማ ሁኔታ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1789 ንዑስ አንቀጽ 3 በሚደነግገው አይነት ለገዠ ካሣወቀው ከአንድ ዓመት በኋላ የውል ይፈፀምልኝ ክስ ያቀረበ መሆኑን ማስረዳት ይጠበቅበታል፡፡

ሻጭ በውሉ መሠረት የቤቱን ይዞታና የባለቤትነት ሰነዶች ለገዥ አስተላልፎ ከሆነ ገዥ ሻጭ በውሉ መሠረት ይፈጽማል የሚለውን ዕምነት የሚያጠናክርና ውሉም በከፊል መፈፀም መጀመሩን የሚያሣይ መሆኑን ከፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2875 እና ከፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2274 ድንጋጌዎች ለመረዳት ይቻላል፡፡ ሰለሆነም ሻጭ የቤቱን ባለሀብትነት ለገዥ ለማስተላለፍ እንደማይፈልግና የቤቱን ይዞታ ሻጭ በመልቀቅ እንዲያስረክበው የከፈለውንም ገንዘብ ገዥ እንዲወስድ በማያሻማ ሁኔታ የፍትብሔር ሕግ ቁጥር 1789 ንዑስ አንቀጽ 3 በሚደነግገው አይነት ለገዥ ያሣወቀ መሆኑን ማስረዳት ይጠበቅበታል፡፡

ሻጭ የቤቱን ሰነዶች ለገዥ አስተላልፎ የቤቱን ይዞታ ይዞ በሚገኝበት ጊዜ የቤቱን ሰነዶች ሻጭ እንዲመልስለት የከፈለውን ገንዘብ እንዲወስድ በማያሻማ ሁኔታና የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1789 ንዑስ አንቀጽ 3 በሚደነግገው አይነት ለገዥ ያሣወቀ መሆኑን ማስረዳት የሚጠበቅበት ሲሆን ከላይ ከተጠቀሱት ሁኔታዎች በአማራጭ ሻጭ ውሉ እንዲፈርስለት ወይም እንዲሰርዝለት በፍርድ ቤት ክስ አቅርቦ በውሉ መሠረት የመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን ገዥ እንዲረዳው ከተደረገ ከአንድ ዓመት በኋላ የውል ይፈፀምልኝ ክስ ገዥ ያቀረበ መሆኑን ወይም በሕግ እውቅና ላለው የሽምግልና ተቋም ሻጭና ገዥ በነበራቸው ድርድር ሻጭ ውሉን ለመፈፀም እንደማይፈልግ ገዢ  እንዲረዳው ከተደረገ ከአንድ ዓመት በኋላ ክሱን ያቀረበው መሆኑን የማስረዳት ግዴታ አለበት፡፡ በአጠቃላይ ሻጭ በገባው የሽያጭ ውል ቃል መሠረት ለመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን በማያሻማ ሁኔታ ለገዥ ካሣወቀውና ገዥም ይህንኑ ከተረዳና ካረጋገጠ ከአንድ ዓመት በኋላ የውል ይፈፀምልኝ ክስ ገዥ ያቀረበ መሆኑን የማስረዳት ግዴታ አለበት፡፡

ሻጭ በውሉ መሠረት ለመፈፀም የማይፈልግ መሆኑን ገዥ ያረጋገጠ መሆኑን ገዥ ውሉ እንዲፈፀምለት ማስጠንቀቂያ መስጠቱንና ማስጠንቀቂያ ከሰጠ በኋላ ሻጭ በውሉ መሠረት አለመፈፀሙን በማየት ብቻ ለማረጋገጥ አይችልም፡፡ ሻጭ ገዥ ማስጠንቀቂያ ከሰጠው በኋላም ቢሆን የተለያዩ ችግሮችን እያነሣ በመካከላቸው ያለውን የመተማመንና የቅን ልቦና ግንኙነት ተጠቅሞ ከአንድ ዓመት በላይ ውሉን ሣይፈፅም የሚቆይበት አጋጣሚ ይኖራል፡፡

ስለዚህ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 ይርጋ ተፈፃሚነት የሚኖረው ገዥ ለሻጭ ማስጠንቀቂያ የሰጠበትን ቀን መነሻ በማድረግና ጊዜውን በማስላት ሣይሆን ሻጭ በውሉ መሠረት የመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን በማያሻማ ሁኔታ ገዥ እንዲያውቀው ያደረገበትን ቀን መነሻ በማድረግ መሆን ይገባዋል፡፡

  1. በሁለተኛ ደረጃ በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 የተደነገገው የይርጋ ጊዜ ተፈፃሚነት የሚኖረው በሻጭና በገዥ መካከል የተደረገው ውል የማይፈፀምበት የመጨረሻ ቀን በጥብቅ የተወሰነ ከሆነ በውሉ የተወሰነ የጊዜ ገደብ ካለፈ ከአንድ ዓመት በኋላ ገዥ የውል ይፈፀምልኝ ክስ ማቅረቡን በማስረዳት እንደሆነ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2875 መሠረታዊ መርህና የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 ድንጋጌዎች ከፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2331ንዑስ አንቀጽ 1 እና 2 ድንጋጌዎች ጋር አጣምሮ በማየት ለመረዳት ይቻላል፡፡
  2. በሶስተኛ ደረጃ የሚነሣው ጥያቄ በዚህ ጉዳይ ተጠቃሽና ተፈፃሚ መሆን ያለበት የይርጋ ሕግ ድንጋጌ የትኛው ነው? የሚለው ነው፡፡ ሻጭ በውሉ መሠረት የመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን ለገዥ በማያሻማ ሁኔታ ያሣወቀ መሆኑን ባላስረዳበት ሁኔታ ወይም የሽያጭ ውሉ የሚፈፀምበትን ጥብቅ የጊዜ ገደብ ባልተገለፀበት ሁኔታ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 የተደነገገው የአንድ ዓመት የይርጋ የጊዜ ገደብ ተፈፃሚነት የለውም፡፡ በልዩ የሕግ ድንጋጌ የተቀመጠዉ የይርጋ ጊዜ ገደብ ተፈፃሚነት በማይኖረው ጊዜ ወይም በልዩ ሁኔታ የተደነገገ የይርጋ የጊዜ ገደብ ከሌለ ውል ይፈፀምልኝ በሚል መነሻ የሚቀርቡ ክርክሮች ላይ ተፈፃሚት ያለው የይርጋ ሕግ ድንጋጌ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1845እንደሆነ ይህንን ድንጋጌ ይዘት በመመርመር ለመረዳት ይቻላል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 38935 ቅጽ 8[13]

ሻጭ የውል ይፍረስልኝ ክስ ለፍርድ ቤት ማቅረቡ ውሉን ለመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን ለገዢ በማያሻማ መንገድ ከማሣወቅ ያለፈ ምክንያትና ውጤት ያለው ተግባር ነው፡፡ ሻጭ ውሉ እንዲፈርስ ሲጠይቅ ውሉ ሕጋዊ በሆነ መንገድ ለማቋቋም የማያስችሉ ጉድለቶች ያሉበት በሁለቱ ተዋዋይ ወገኖች እንደ ሕግ ሆኖ ሊገዙበት የማይገባ መሆኑን የሚያሣዩ የውሉን ሕልውና ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባና የውል ሕጋዊነት በፍርድ ቤት ተመርምሮ ፈራሽ እንዲባል ወይም እንዲሠረዝ የሚቀርብ ነው፡፡ የውሉ ሕጋዊነትና ሕልውና ጥያቄ ተነስቶበት በፍርድ ቤት በሚመረመርበት ጊዜ ሂደት ገዢ ውሉ ሕጋዊ መሆኑን ከማሣየትና ከማስረዳት አልፎ ውሉ በግዳጅ እንዲፈጽምለት የመጠየቅ ግዴታ አይኖርበትም፡፡

ከዚህ አንፃር ውሉ በፍርድ ቤት ፈራሽ እንዲሆን ወይም እንዲሰረዝለት በውሉ የሚገደድበት ሁኔታ ይቋረጣል፡፡ በሌላ በኩል በክርክሩ ከተረታ ገዢ ሕጋዊ ተፈፃሚነትና አስገዳጅነት ባለው ውሉ ንብረቱን የገዛ መሆኑ ከሻጭ ጋር ባደረገው የውል ሰነድ ብቻ ሣይሆን በፍርድ ቤት ውሣኔ የተረጋገጠለት የፍርድ ባለመብት ይሆናል፡፡ ስለሆነም ገዢ ፍርድ ቤቱ ሕጋዊነቱንና አስገዳጅነቱን መርምሮ በፍርድ ያረጋገጠውን ውል እንዲፈጽምለት ሻጭን የመጠየቅ መብቱ በፍርድ ከተረጋገጠበት ጊዜ ጀምሮ በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 384/ሀ/ በተደነገገው አስር ዓመት ጊዜ ውስጥ እንጂ በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 በተደነገገው የአንድ ዓመት የጊዜ ገደብ የሚገደብ አይደለም፡፡ ስለዚህ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀስ 3 የተቀመጠው የጊዜ ገደብ በዚህ ጉዳይ አግባብነት የለውም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 39725 ቅጽ 8[14]

ይርጋ መነሻ ጊዜ(የ—)

ይርጋ መቆጠር የሚጀምርበት ጊዜ

የይርጋ ቀን መቆጠር የሚጀምረው ግዴታውን ለመጠየቅ ተገቢ ከሆነው ወይም ውሉ የሚሰጠው መብት ከተሰራበት ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡

የሥራ ውል የተቋረጠበትና የስንብት ደብዳቤ የተሰጠበት ቀን ከተለያየ ይርጋ መቆጠር የሚጀምረው ደብዳቤው ለሠራተኛው ከተሰጠበት ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 94931 ቅጽ 16፣[15] ፍ/ብ/ህ/ቁ. 1846

በፍትሐ ብሔር ስነ-ስርዓት ህጉ የሚገኙት የጊዜ ገደቦች አቆጣጠር የሚመራው በፍትሐ ብሔር ህግ ባሉት የጊዜ አቆጣጠር ደንቦች ነው፡፡

ጉዳዩ በሌለበት ታይቶ ውሳኔ የተሰጠበት ወገን ውሳኔው እንዲነሳለት በፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 78/1/ መሰረት በአንድ ወር ውስጥ የሚያቀርበው ጥያቄ የአንድ ወር ጊዜ መቆጠር የሚጀምረው ውሳኔ መሰጠቱን ከተረዳበት ቀን ጀምሮ ነው፡፡ ሆኖም የመጀመሪያው ቀን ለይርጋው ጊዜ መቆጠር መነሻ አይሆንም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 76601 ቅጽ 13፣[16] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 78/1/

በወራሾች መካከል ውርስ እንዲጣራ አቤቱታ መቅረብ ያለበት በሶስት ዓመት ጊዜ ውስጥ ሲሆን ይህም ጊዜ መቆጠር የሚጀምረው አንደኛው ወራሽ የውርሱን ንብረት በእጁ ካደረገበት እንጂ ስመ ሀብቱን በስሙ ካዞረበት ጊዜ ጀምሮ አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 52407 ቅጽ 11፣[17] ፍ/ህ/ቁ. 1000/1/

ከውርስ ሃብት ጋር በተያያዘ ወራሽ የሆነና አካለ መጠን ያልደረሰ ሰው ላይ የይርጋ ጊዜ ሊቆጠር የሚገባው አካለ መጠን ከደረሰበት ጊዜ አንስቶ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 57114 ቅጽ 11[18]

ይዞታን አስመልክቶ ከሚነሳ የሁከት ይወገድልኝ አቤቱታ ጋር በተያያዘ ተፈፃሚ የሚሆነው የይርጋ ጊዜ መቆጠር ያለበት አቤቱታ አቅራቢው የይዞታ መብቱን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ከሚመለከተው አካል ካገኘበት ቀን ጀምሮ እንጂ አቤቱታ የቀረበበት ድርጊት መፈፀም ከጀመረበት ዕለት አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 60392 ቅጽ 11፣[19] ፍ/ብ/ህ/ቁ. 1140፣ 1149፣ 1146/1/፣ 1144/2/

[1] አመልካች አቶ አብደራዛቅ ሀሚድ እና ተጠሪ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጥቅምት 05 ቀን 2002 ዓ.ም.

[2] አመልካች አንበሳ ኢንሹራንስ ኩባንያ እና ተጠሪ የኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት ጥር 05 ቀን 2007 ዓ.ም.

[3] አመልካች አቶ አብደራዛቅ ሐሚድ እና ተጠሪ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጥቅምት 05 ቀን 2002 ዓ.ም.

[4] አመልካች አሊ ቃሌብ አህመድ እና ተጠሪ እነ አቶ ሚሊዮን ተፈራ /3 ሰዎች/ መጋቢት 18 ቀን 1999 ዓ.ም.

[5] አመልካች ወ/ሮ ድንቄ ተድላ እና ተጠሪ እነ አቶ አባተ ጫኔ መጋቢት 20 ቀን 1999 ዓ.ም.

[6] አመልካች የኪራይ ቤቶች አስተዳደር ድርጅት እና መልስ ሰጪ ሚ/ር ቢሮኒ አቲክፖ ሐምሌ 19 ቀን 1997 ዓ.ም.

[7] አመልካች የኢትዮጵያ መድን ድርጅት እና ተጠሪ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ግንቦት 12 ቀን 2000 ዓ.ም.

[8] አመልካች የኢትዮጵያ መድን ድርጅት እና ተጠሪ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ግንቦት 12 ቀን 2000 ዓ.ም.

[9] አመልካቾች እነ ወ/ሮ አለዊያ ዑመር /7 ሰዎች/ እና ተጠሪ አቶ ሐሺም ሁሴን የካቲት 26 ቀን 2006 ዓ.ም.

[10] አመልካች የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይሌ ኮርፕሬሽን እና ተጠሪ አቶ አማረ ገላው ሀምሌ 30 ቀን 2002 ዓ.ም.

[11] አመልካች እነ አቶ ይሌማ አንበሴ /4 ሰዎች/ እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ እመቤት መንገሻ /5 ሰዎች/ መጋቢት 6 ቀን 2002 ዓ.ም.

[12] አመልካች ወ/ሮ አሌማዝ ተሰማ እና ተጠሪ እነ አቶ በየነ ወ/ሚካኤሌ/2 ሰዎች/ መጋቢት 22 ቀን 2002 ዓ.ም.

[13] አመልካች እነ አቶ ወልደፃድቅ ብርሃኑ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ አቶ ስንታየሁ አያሌው መጋቢት 3 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም.

[14] አመልካቾች እነ ወ/ሮ ዓለምሸት ካሣሁን /3 ሰዎች/ እና ተጠሪ አቶ ሽመልስ እንዳለ ሐምሌ 23 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም.

[15] አመልካች ወ/ሮ ጥሩወርቅ መንግስቴ ተጠሪ የተገጣጣሚ ህንፃ አካላት ማምረቻ ድርጅት የካቲት 14 ቀን 2006 ዓ.ም.

[16] አመልካች አቶ ሽመልሽ አማረ እና ተጠሪ አቶ አማረ መኮነን ሰኔ 18 ቀን 2004 ዓ.ም.

[17] አመልካቾች እነ ወ/ሮ ውልታ ደስታ ወ/ማሪያም /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ ወ/ሮ እቴቴ ደስታ ኅዳር 27 ቀን 2003 ዓ.ም.

[18] አመልካች ወ/ሮ ሃና ፀጋዬ እና ተጠሪ ወ/ት ጣዕሙ ደስታ ግንቦት 3 ቀን 2003 ዓ.ም.

[19] አመልካች አቶ ጌትነት የኔው እና ተጠሪ አቶ ኢዩብ ቢንያም ወ/ቢኒያም ታህሣሥ 26 ቀን 2003 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

‘እንዳልተሰጠ የሚቆጠር ውሳኔ’ ምን ዓይነት ነው?

$
0
0

በህግ አግባብ የተቋቋመ ፍርድ ቤት ግራ ቀኙን አከራክሮ ውሳኔ ከሰጠ በኋላ ለአፈጻጸም ሲቀርብ ውሳኔው እንዳልተሰጠ ተቆጥሮ አፈጻጸሙን በያዘው ፍርድ ቤት ዋጋ የሚያጣበት የህግ መሰረት አለ? ከሰበር ችሎት ውሳኔዎች ለመረዳት እንደሚቻለው አንድ ውሳኔ በሶስት መንገዶት እንዳልተሰጠ ሊቆጠር ይችላል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አንዱ የስረ ነገር የዳኝነት ስልጣን አለመኖር ነው፡፡ ምንም እንኳን ችሎቱ በአንድ መዝገብ ላይ ይህን አቋም ቢያራምድም በሌሎች ሁለት መዝገቦች ላይ ግን ራሱን በመቃረን የስረ ነገር የዳኝነት ስልጣን የፍርድ ቤትን ውሳኔ እንዳልተሰጠ እንደማያስቆጥረው የህግ ትርጉም ሰጥቷል፡፡ ሌሎቹ ሁለት መንገዶችና የችሎቱ ተቃርኖ የታየባቸው መዝገቦች የሚከተሉት ናቸው፡፡

  1. የሥረ ነገር የዳኝነት ስልጣን በሌለው ፍርድ ቤት የተሰጠ ውሳኔ

አንድ ፍርድ ቤት ጉዳዩን ከማየቱ በፊት የስረ ነገር የዳኝነት ስልጣን ያለው መሆኑን ማረጋገጥ ያለበት ሲሆን የስረ ነገር የዳኝነት ስልጣን በተከራካሪ ወገኖች ባይነሳም በማናቸውም የክርክር ደረጃ ፍርድ ቤቱ በራሱ ሊያነሳው የሚገባው ጉዳይ መሆኑ ከፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 9 እና 231/1/ ሰ ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ የምንገነዘበው ጉዲይ ነው፡፡ የሥረ ነገር የዳኝነት ስልጣን በሌለው ፍርድ ቤት የተሰጠ ውሳኔ ደግሞ በመርህ ደረጃ እንዳልተሰጠ የሚቆጠር ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 64703 ቅጽ 12፣[1] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 9፣ 231/1/ ሰ

  1. ችሎት ለማስቻል በህጉ የተቀመጠው የዳኞች ቁጥር ባልተሟላበት ሁኔታ የሚሰጥ ውሳኔ

ጉዳዮች በሥነ ሥርዓት ሕጉ መሠረት የሚመሩበት አይነተኛ አላማ ክርክሮችን ፍትሃዊ በሆነ እና ሥርዓት ባለው መንገድ በመምራት በአጭር ጊዜ እና በአነስተኛ ወጭ እንዲቋጩ ማድረግ ስለመሆኑ ይታመናል፡፡ ይህንኑ የሥነ ሥርዓት ሕጉን አላማ ለማሳካት ደግሞ በሕጉ የተመለከቱትን የስነ ሥርዓት ድንጋጌዎችን እንደየአግባብነታቸው መከተልን የግድ ይላል፡፡ በስነ ሥርዓት ሕጉ የተመለከቱት ድንጋጌዎችን እንደየአግባብነታቸው ያለመከተል በተከራካሪ ወገኖች መሰረታዊ መብት ላይ አሉታዊ ውጤት ማስከተሉ አይቀሬ ነው፡፡ ስለሆነም በስነ ስርዓት ሕጉ የተመለከቱት ድንጋጌዎች ተፈፃሚነት ሊኖራቸው የሚገባው ለጉዳዩ አግባብነት ሲኖራቸው እንጂ በዘፈቀደ ሊሆን አይገባም፡፡

ድንጋጌዎቹ አግባብነት ያላቸው ስለመሆኑ ከመለየቱ በተጨማሪ በጉዳዩ ላይ ተገቢነት አለው የሚለውን ትዕዛዝ ወይም ውሣኔ የሚሰጠው ችሎትም በሕጉ አግባብ የተመለከተው የዳኞች ቁጥር የተሟላ ሊሆን ይገባል፡፡ በሕጉ አግባብ ሊሟላ የሚገባው የዳኞች ቁጥር ሳይሟላ የሚሰጠው ትእዛዝ ወይም ውሣኔ እንደተሰጠ የማይቆጠርና ሕጋዊ ውጤት ሊኖረው የሚገባ አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ 73696 ቅጽ 13[2]

  1. በሞተ ሰው ውክልና ክርክር ተደርጎ የተሰጠ ውሳኔ

በሞተ ሰው ስም ቀደም ብሎ የተሰጠን ውክልና በመያዝ የሚቀርብ ክስ፣ የሚደረግ ክርክር እና የሚሰጥ ውሣኔ ህጋዊ ዕውቅናና ውጤት ሊሰጠው የማይገባው ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 95587 ቅጽ 17፣[3] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 57፣ ፍ/ህ/ቁ. 2232/1/

ከሰ/መ/ቁ. 64703 ጋር ተቃርኖ

አንድ ፍርድ ቤት የሰጠው ውሣኔ በሕግ ከተሰጠው የስረ ነገር የዳኝነት ስልጣን ውጭ የሆነ ጉዳይ በማየት የሰጠው ቢሆንም፣ ይህ ውሣኔ በይግባኝ ታይቶ እንዲታረም ካልተደረገ በስተቀር በፍ/ሥ/ሥ/ሕግ ቁጥር 212 በጉዳዩ ላይ አስገዳጅነት ያለውና የመጨረሻ ውሣኔ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 85718 ቅጽ 15[4]

በሕግ አግባብ በፍ/ቤት የተሰጠን ውሣኔ የሞራልን ወይም የሕሊናን አስተሳሰብ መሠረት በማድረግ ዋጋ አልባ ሆኖ እንዲቀር ማድረግ በየትኛውም መለኪያ ተቀባይነት የሚኖረው አይደለም፡፡

ሰበር መ/ቁ. 38041 ቅጽ 8[5]

[1] አመልካች ሻምበል ለታይ ገ/መስቀል እና ተጠሪ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ የወረዳ 1 አስተዳደር ጽ/ቤት ሐምሌ 29 ቀን 2003 ዓ.ም.

[2] አመልካች ወ/ሪት ሃና አበባው እና ተጠሪ አቶ አብዱ ይመር /በሌለበት/ ሚያዝያ 9 ቀን 2004 ዓ.ም.

[3] አመልካች ወ/ሮ ሐዋ በከር እና ተጠሪ እነ አቶ ቶፊቅ መሀመድ 2 ሰዎች ጥቅምት 28 ቀን 2007 ዓ.ም.

[4] አመልካች አቶ ቴዎድሮስ አማረ እና ተጠሪ አቶ አዲሱ ፍሰሃ ሰኔ 03 ቀን 2005 ዓ.ም.

[5] አመልካች ታደሰ ገ/መስቀል ተጠሪዎች እነ ሙሉጌታ ዘካርያስ /7 ሰዎች/ መጋቢት 22 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

ተከሳሽን የሚጠቅም ቅጣት- የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0

በወንጀል የተከሰሰ ሰው አዲስ የወንጀል ህግ ከመውጣቱ በፊት በተፈፀመ ወንጀል ከተፈረደበት እና ሆኖም ግን ወንጀሉ በተፈፀመበት ጊዜ ስራ ላይ ከነበረው ወንጀል ህግ ይልቅ አዲሱ ህግ ለተከሳሹ ቅጣትን የሚያቀልለትና ተከሳሹን የሚጠቅም ሆኖ ከተገኘ ይሄው በአዲሱ ህግ ላይ ያለው ቅጣት የሚፈጸምበት ስለመሆኑ ከወንጀል ህጉ ቁ. 6 ድንጋጌ ይዘት የምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 95438 ቅጽ 6፣[1] ወ/ህ/ቁ. 6

የሰበር ሰሚ ችሎት ውሳኔ ተፈጻሚነት

በአንድ ወንጀል ተመሳሳይ የጥፋተኝነትና የቅጣት ውሳኔ ከተላለፈባቸው ተከሳሾች መካከል አንደኛው ባቀረበው የሰበር አቤቱታ መነሻነት ተጠቃሚ የሚያደርጋቸው ፍርድ ከተሰጠ ፍርዱ የሰበር አቤቱታ ላልጠየቁት ሆነ ጠይቀው አቤቱታቸው በአጣሪ ችሎት አያስቀርብም ተብሎ ውድቅ ለተደረገባቸው ሌሎች ተከሳሾችም ጭምር ተፈጻሚነት አለው፡፡

በተመሣሣይ የወንጀል ህግ ድንጋጌ ጥፋተኛ ተብለውና በወንጀሉ የነበራቸው ተሣትፍ እና ሌሎች ግላዊ ሁኔታዎች ተመሣሣይ ሆኖ በመገኘቱ ተመሣሣይ የሆነ የቅጣት ውሣኔ የተላለፈባቸው ሰዎች፣ የአንደኛው የሰበር አቤቱታ የሚጣራ የህግ ነጥብ ያለው መሆኑ ተገልጾ ለሰበር ችሎት ሰለቀረበና በውሣኔው ላይ መሠረታዊ የህግ ስህተት ያለበት መሆኑ ተገልጾ በሚሰጠው ፍርድ ተጠቃሚ የሚሆንበት የሌላኛው የሰበር አቤቱታ የሰበር አጣሪ ችሎት ለሰበር አያስቀርብም ተብሎ ውድቅ ስለተደረገበት ብቻ የፍርዱ ተጠቃሚ የማይሆንበትን አግባብ መከተል በህገ መንግስቱ አንቀፅ 25 እና በወንጀል ህጉ አንቀጽ 4 የተደነገገውን የእኩልነት መርህ የሚጥስና የሰበርን መሠረታዊ ዓላማ የማያሳካ ይሆናል፡፡

የወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት አንቀጽ 196 “የተፈረደባቸው ሰዎች ብዙ ሆነው አንድ ብቻ ይግባኝ ሲያቀርብ” የሚል ርዕስ ያለው ሲሆን የድንጋጌው ንዑስ አንቀጽ 1 ቃል በቃል ሲነበብ “ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት ያቀረበው ይግባኝ ስለተፈረደባቸው ብዙ ሰዎች የሚመለከት ሆኖ ይግባኝ ያለው ግን የተፈረደበት አንድ ሰው ብቻ በሆነ ጊዜ ከዚህ በታች የተመለከተው ሲሆን ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት የሚሰጠው ፍርድ ይግባኝ ያላሉትም ሰዎች ይግባኝ እንዳሉ ተቆጥሮ ይፈጸምላቸዋል ለማለት የሚቻለው፤ /ሀ/ በይግባኝ የተሰጠው ፍርድ ይግባኝ ባዩን የሚጠቅም በሆነ ጊዜና /ለ/ ተከሳሾች ይግባኝ ቢሉ ኖሮ በፍርድ እነርሱም ሊጠቀሙ ይችሉ ነበር የሚያሰኝ ሆኖ ሲገኝ ነው” የሚል ይሁንታ ያለው ነው፡፡

ይህንን ድንጋጌ አሁን ላለው የሰበር ስርዓት ለመጠቀም ካለው የሰበር ችሎት አደራጃጀትና አሰራር ጋር  በሚጣጣምና የሰበርን መሰረታዊ ዓላማ ሊያሳካ በሚችል መንገድ መተርጎምና ስራ ላይ ማዋል ይጠይቃል፡፡ ብዙ ተከሳሾች በአንድ ወንጀል የወንጀል ስራው ተካፋይና ግብረ አበር ሆነዋል ተብለው ክስ ቀርቦባቸውና፣ ጉዳዩን በመጀመሪያ ባየው ፍርድ ቤት እና በይግባኝ ባየው ፍርድ ቤት ወይም ይግባኝ ሰሚ ችሎት የተሰጠው የጥፋተኝነትና የቅጣት ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት አለበት በማለት አንደኛው ተከሳሽ የሰበር አቤቱታ አቅርቦ፣ አቤቱታው ለሰበር ችሎት ያስቀርባል ተብሎ በሰበር ችሎት ታይቶ፣ ጉዳዩን በመጀመሪያ ደረጃ ወይም በይግባኝ አይቶ ውሳኔ የሰጠው ፍ/ቤት የጥፋተኝነት ወይም የቅጣት ውሳኔ ወይም የጥፋተኝነትና የቅጣት ውሳኔው መሰረታዊ ህግ ስህተት አለበት ተብሎ ከተሻረ፣ ከተሻሻለ ወይም ከተለወጠና የሰበር ችሎት በመሻር፣  በማሻሻል ወይም በመለወጥ የሰጠው ውሳኔ የሰበር አቤቱታ ያላቀረቡትን ሌሎች በአንድ ጉዳይ የተከሰሱ ሰዎችን የሚጠቅም ሆኖ በተገኘ ጊዜ፣ ሰዎቹ ፍርዱን በመቃወም የሰበር አቤቱታ ባያቀርቡም ሰበር ችሎት በሰጠው ውሳኔ ወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ህግ ቁጥር 196 ንዐስ አንቀጽ 1 መሰረት ተጠቃሚ እንደሆኑ በሚያደርግ አግባብ ድንጋጌው መተርጎምና ስራ ላይ መዋል አለበት፡፡

በአንድ ወንጀል አድራጎት በወንጀል ህግ ስለወንጀል ተካፋይነት አድራጊነት ወይም ስለግብረአበርነት በተደነገጉት መሰረት በአንድ ላይ ፈጽመዋል ተብለው ክስ ከቀረበባቸው ጉዳዩን በመጀመሪያ ደረጃ ባየውና በይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት የጥፋተኝነትና የቅጣት ውሳኔ የተወሰነባቸው ሰዎች ብዙ ሰዎች ሁሉም በግላቸው የሰበር አቤቱታ አቅርበው የሰበር መዝገብ አስከፍተው ከፊሎቹ ያቀረቡት የሰበር አቤቱታና ያስከፈቱት የሰበር መዝገብ በሰበር ችሎት የሚቀርብ መሠረታዊ የህግ ስህተት ጭብጥ የለውም ተብሎ በአዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀፅ 22 መሠረት በሰበር አጣሪ ችሎት ውድቅ ቢደረግና ቢዘጋ የከፊሎቹ ወይም አንደኛው ተከሳሽ ያቀረበው የሰበር አቤቱታ በሰበር የሚጣራ መሠረታዊ የህግ ጭብጥ አለው ተብሎ ለሰበር ችሎት ቀርቦ የሰበር ችሎቱ የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኃላ የጥፋተኝነት ውሣኔውን ወይም የቅጣት ውሳኔውን ወይም የጥፋተኛነትና የቅጣት ውሣኔውን መሠረታዊ የህግ ስህተት አለበት በማለት የሰበር ችሎት ከሻረው፣ ካሻሻለው ወይም ከለወጠውና ውሳኔው የሰበር አቤቱታ አቅርበው የሰበር ማጣሪያ ችሎት የሚጣራ መሠረታዊ የህግ ስህተት ጭብጥ የለውም ብሎ አቤቱታውን ውድቅ ያደረገባቸውን ሰዎች የሚጠቅም ሆኖ በተገኘ ጊዜ የወንጀለኛ መቅጫ ሥነሥርዓት ህግ ቁጥር 196 ንዐስ አንቀፅ 1 ድንጋጌ ተፈፃሚ መሆን ይገባዋል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 101056 ቅጽ 18፣[2] ኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ህገ መንግስት አንቀጽ 25፣ ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 196

የዋስትና መብት አወሳሰን

በመርህ ደረጃ የተሻረ ሕግ ተፈፃሚነት የሌለው ሲሆን በተሻረ ሕግ ክስ ማቅረብ ደግሞ የመርሁ ልዩ ሁኔታ ነው፡፡ የተሻረውም ሕግ ተጠቅሶ በተከሳሹ ላይ ክስ የሚቀርበው ወንጀሉ ተሰርቷል በተባለ ጊዜ ሕጉ ሥራ ላይ ስለነበርና ተከሣሹም ያውቀዋል ተብሎ ስለሚገመትና በሚያውቀው ሕግ መሠረት መከራከር እንዳለበት የሕግ መርህ /Rule of legality/ ስለሚያስገድድ ነው፡፡ ከዚህም መገንዘብ የሚቻለው የተሻረው ሕግ የሚጠቀሰው ተከሳሹ ክርክሩን በአግባቡ ለመምራት እንዲያስችለው እንጂ ከዚህ ያለፈ ውጤት የሌለውና መጨረሻም ላይ ቅጣት የሚወሰነው ሥራ ላይ ባለ ሕግ ተመስርቶ መሆኑን ነው፡፡

የዋስትና ጉዳይ በዋናነት የሚታየው ቅጣትን መሠረት አድርጎ ነው፡፡ ተከሳሽ የተከሰሰው የዋስትና መብት በሚከለክል ድንጋጌ ቢሆንም ድንጋጌው የሚጠቀሰው ክርክሩን በአግባቡ ለመምራት ታስቦ እንደሆነ ሕጉ ይዞት የተነሳውን ዓላማ መገንዘብ ከተቻለ የዋስትናው ጉዳይ መታየት የሚገባው ሊወሰንበት ከሚችለው ቅጣት አኳያ መሆን እንዳለበት ይታመናል፡፡ ክርክሩ እልባት ካገኘ በኋላ ተከሳሹ የሚቀጣው በአዲሱ ሕግ መሠረት እንደሆነ ከወዲሁ በግልጽ መገንዘብ ከተቻለ ክርክሩ እስከሚጠናቀቅ ድረስ በእሥር ይቆይ ማለት ሕግ አውጭው የዋስትና መብት ሊከለክላቸው ያልፈለገውን ተከሣሾች የዋስትና መብት እንደመከልከል የሚቆጠርና ሕጉም የታለመለትን ዓላማና ግብ እንዳይመታ የሚያደርግ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 34077 ቅጽ 7[3]

[1] አመልካች አቶ ሰለሞን ደሣለኝ እና ተጠሪ የደቡብ ክልል ዐ/ህግ ግንቦት 07 ቀን 2006 ዓ.ም.

[2] አመልካች አቶ አይሸሽም ገብሬ እና ተጠሪ የፌደራል የሥነ ምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሐምሌ 30 ቀን 2007 ዓ.ም.

[3] አመልካች አቶ ሰይድ ይመር እና ተጠሪ የአማራ ክልል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን መጋቢት 9 ቀን 2000 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

ደሀ ደንብ- የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0

ዳኝነት ሳይከፈል፣ በነፃ መዝገብ ማስከፈት

ክስ ለማቅረብ የፈለገ ወገን ከፍርዱ ለሚያገኘው የዳኝነት አገልግሎት መክፈል የሚገባውን የዳኝነት ገንዘብ ለመክፈል የሚያስችል የገንዘብ አቅም የሌለው ከሆነ ክሱን ያለዳኝነት ገንዘብ በደሀ ደንብ መሠረት የማቅረብ መብት እንዳለው በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 215 ተደንግጓል፡፡ ክሱን የሚያቀርበው ወገን ድሀ በመሆኑ ምክንያት የዳኝነት ገንዘብ ሳይከፍል ክሱን አቅርቦ እንዲያሰማ ሊፈቅድለት ይገባል? የሚለው ጉዳይ ሊለይ የሚችልበት ዝርዝር አፈፃፀም ደንቡም ፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 467 እና ተከታዩ ድንጋጌዎች ተመልክቷል፡፡

እነዚህ ደንቦች ተፈፃሚነታቸው ክስ ለማቅረብ በፈለገ የተፈጥሮ ሰውም ሆነ በሕግ ሰውነት ያላቸው ወገኖችም ጭምር ነው፡፡

በዚህም መሠረት ድሀ ነኝ፤ መብቴን ለማስከበር ያለኝ ፍላጐቴ በዳኝነት ገንዘብ እንቅፋት ምክንያት ሊሰናከል አይገባም፡፡ ስለሆነም በድሀ ደንብ መሠረት ክሱን በነፃ እንዳሰማ ይፈቀድልኝ የሚል ማናቸውም ከሳሽ ድሀ መሆኑን ሊያመለክት የሚችል የሚገኝበትን የገንዘብ አቋም ማረጋገጥ ይገባዋል፡፡ ይህም ከሳሹ የሚገኝበት የገንዘብ አቋም ከተረጋገጠ በኋላ ለክሱ ሊከፈል የሚገባው የዳኝነት ገንዘብ መጠን ከሳሹ ከሚገኝበት የገንዘብ አቋም አኳያ ተገናዝቦ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 467 መሠረት ድሀ የመሆኑና ያለመሆኑ ጉዳይ ሊለይ ይገባል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 79555 ቅጽ 14፣[1] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ 215፣ 467

አንድ ሰው በፍርድ ሊያልቅ የሚገባው ጉዳይን ፍርድ ቤት ይዞ ሲቀርብ የዳኝነት አገልግሎት ክፍያ መክፈል ያለበት መሆኑን የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 215፣ ከ467 እስከ 479 ድረስ የተደነገጉት ድንጋጌዎች ያሳያሉ፡፡ የዳኝነት አገልግሎት መክፈል የማይችል ሰው ክስ ለማቅረብ የሚችልበት አግባብ ስለመኖሩም ተጠቃሽ ድንጋጌዎች ያስገነዝባሉ፡፡ አንድ የዳኝነት አገልግሎት ክፍያ ለመክፈል የማይችል ሰው በደሃ ደንብ ክስ ለማቅረብ የሚችል ሲሆን ለመክፈል አቅም እያለው ክስ ያቀረበ መሆኑ ከተረጋገጠ ግን መዝገቡ እንደሚዘጋ፣ የተዘጋ መዝገብ ደግሞ የዳኝነት አገልግሎት ክፍያ /ገንዘቡን/ ለመክፈል ዝግጁ እስከሆነ ድረስ የሚንቀሳቀስለት መሆኑን የሥነ ሥርዓት ሕጉ ድንጋጌዎች መንፈስና ይዘት ያስገነዝባሉ፡፡

ሰ/መ/ቁ. 52942 ቅጽ 12፣[2]  ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ 215፣ 467-479

ይግባኝ

ዳኝነት ሳይከፈል በነፃ ለመክሰስ እንዲፈቀድ በቀረበ ጥያቄ ላይ ሊሰጥ የሚችለው ትእዛዝ እንደነገሩ ሁኔታ ሁለት ዓይነት ነው፡፡ አንደኛው ከሣሽ የዳኝነት ገንዘብ ለመክፈል የሚያስችለው የገንዘብ አቅም የሌለው ስለሆነ እንደ ጥያቄው የዳኝነት ገንዘብ ሳይከፍል በነፃ ፋይል ከፍቶ ክሱን ለማቅረብ ይችላል የሚለው ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ ከሣሹ ድሃ ያለመሆኑ ስለተረጋገጠ ተገቢውን የዳኝነት ገንዘብ ካልከፈለ በቀር በነፃ ፋይል ከፍቶ ክሱን ለማቅረብ አይችልም የሚለው ነው፡፡

በመጀመሪያው አኳኋን ትእዛዝ በተሰጠ ጊዜ በዚህ ትእዛዝ መሠረት ፋይሉ ተከፍቶ ክርክሩ የሚቀጥል ነው፡፡ የክርክሩ ውጤት የሚታወቀው ግራ ቀኙ በሚያቀርቡት የፍሬ ነገርና የሕግ ክርክር ማስረጃ መሠረት ነው፡፡ በመጨረሻው የክርክር ውጤት ተከሣሹ ባይስማማ ክርክሩ ከመጀመሩ በፊት ክሱ ዳኝነት ሳይከፈልበት በነፃ እንዲከፈት መደረጉ የሕግ ድጋፍ አልነበረውም የሚለውን እንደ አንድ የይግባኝ ምክንያት በማድረግ በውሣኔው ላይ ካለው ቅሬታ ጋር አዳምሮ ማቅረብ ይኖርበታል እንጂ ከሥረ-ነገሩ ፍርድ በፊት የይግባኝ አቤቱታ የማቅረብ መብት አይኖረውም፡፡ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ. 320/3/ የተመለከተው ድንጋጌም በዚህ አኳኋን በሚቀርበው የይግባኝ አቤቱታ ላይ ክልከላ ለማድረግ ነው፡፡

በሌላ በኩል “ድሀ ያለመሆንህ ተረጋግጧል፡፡ የዳኝነት ገንዘብ ካልከፈልክ በቀር ፋይል አይከፈትም” ለተባለው ከሣሽ ግን ይህ ዓይነቱ ትእዛዝ የመጨረሻ ነው፡፡ ሌላ የሚጠበቅ የሥረ-ነገር ፍርድ የለውም፡፡ ስለሆነም የዳኝት ገንዘብ ለመክፈል አቅም ሳይኖረኝ ክርክሬና ማስረጃዬ በአግባቡ ሳይታይ አቅም እንዳለኝ ተቆጥሮ የዳኝነት ገንዘብ ክፈል መባሌ ተገቢ አይደለም የሚል ከሆነ የተሰጠው ትእዛዝ የመጨረሻ እንደመሆኑ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 320/1/ መሠረት የይግባኝ አቤትታ የማቅረብ መብት አለው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 23744 ቅጽ 6፣[3] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 320

[1] አመልካች ቤተልሄም ፋርማሲ ቲዩካል ኃ/የተ/የግል/ማህበር ተጠሪ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ታህሳስ 02 ቀን 2005 ዓ.ም.

[2] አመልካች አቶ ገብሩ ኮሬ እና ተጠሪ አቶ አመዲዮ ፌዴሬቺ ጥቅምት 18 ቀን 2003 ዓ.ም.

[3] አመልካች አቶ በቀለ በድዬ እና መልስ ሰጪ እነ የወጋገን ባንክ አዋሳ ቅርንጫፍ /3 ሰዎች/ ሐምሌ 26 ቀን 1999 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

Ethiopia Devalues Currency by 15 Percent to Boost Exports – The New York Times

ደምዳሚ (ድምዳሜ) ማስረጃ ምንድነው?

$
0
0
  1. የተሟላና ሙሉ ዕምነት የሚጣልበት ማስረጃ

የልዩ አዋቂ /expert/ የሚደርስበት የመጨረሻ አስተያየት ከሚኖረው ሙያዊ ዕውቀት አድማስ፣ ከሚታገዝበት መሣሪያና ከመሳሰሉት ጋር የተሟላና ሙሉ ዕምነት የሚጣልበት ማስረጃ /conclusive evidence/ ሊሆን ስለማይችል በዓይን ምስክሮች የተነገረን ፍሬ ነገር ለማስተባበል የሚያበቃ አቅም አይኖረውም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 43453 ቅጽ 12[1]

የትራፊክ ፖሊስ የአደጋ ፕላን ሪፖርት የባለሙያ ሙያዊ አስተያየትን በወረቀት ላይ ስዕላዊ በሆነ መንገድ የሚያስቀምጥ በባለሙያ የሚረጋገጥ ሰነድ በመሆኑ እንደ ማንኛውም የልዩ አዋቂ የምስክርነት ቃል በተገቢው መንገድ ሊመዘን የሚገባው የማስረጃ አይነት እንጅ ሁልጊዜ ድምዳሜ ማስረጃ (Conclusive Evidence) ያለመሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 92141 ቅጽ 17[2]

  1. አሳሪ ማስረጃ

በአስተዳደር አካል የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለቤት ነው ተብሎ የምስክር ወረቀት መስጠት ማስረጃውን ደምዳሚ ወይም አሳሪ (Conclusive Evidence) የሚያደርገው አይደለም፡፡ ይልቁንም ይኸው ማስረጃ የተሰጠበት አግባብ በፍ/ህ/ህ/ቁ. 1195 ድንጋጌ ስር በተመለከቱት ሁኔታዎች መሰረት ስለመሆኑ ማስረዳት ከተቻለ በፍ/ህ/ቁ. 1195 ስር የተመለከተው ሕጋዊ ግምት ሊስተባበል የሚችል (rebuttable legal presumption) መሆኑን ከድንጋጌዎቹ ይዘትና መንፈስ የምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 64014 ቅጽ 13[3]

  1. ማስተባበያ ሊቀርብበት የማይችል ወሳኝ ማስረጃ

አንድ ለማይንቀሳቀስ ንብረት የተሰጠ የባለሃብትነት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ባለሃብትነትን በተመለከተ የህግ ግምት የሚያሰጥ ቢሆንም በሌላ ተቃራኒ ማስረጃ ሊስተባበል፣ በተቃራኒው ከሚቀርቡት ማስረጃዎች ጋር ሊመዘን የሚችል እንጂ እንጅ ማስተባበያ ሊቀርብበት የማይችል ወሳኝ /conclusive evidence/ ያለመሆኑን መገንዘብ ይቻላል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 67011 ቅጽ 13[4]

  1. የመጨረሻ ማስረጃ

የልጅነት ሁኔታ መኖሩን ማስረዳት ከተቻለ ፍ/ቤት ልጅ ነው ሲል የሕግ ግምት ሊወስድ የሚችል መሆኑን የተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አንቀጽ 157/1/ ያመለክታል፡፡ ከአንቀፁ መረዳት እንደሚቻለው የልጅነት ሁኔታ መኖሩን ማረጋገጥ የመጨረሻ ማስረጃ (conclusive evidence) ሳይሆን የሕግ ግምት ብቻ ነው፡፡ ግምቱም ቢሆን አስገዳጅነት ያለው የሕግ ግምት አይደለም፡፡ ግምቱን የሚቃወም ወገን ማስረጃ በማቅረብ ማፍረስ እንደሚችል ንዑስ አንቀፅ 2 ይደነግጋል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 42648 ቅጽ 10[5]

  1. ክርክር ሊነሳበት የማይችል ማስረጃ

ልጅነት የሚረጋገጥበት ዋናው ማስረጃ የልደት ምስክር ወረቀት እንደሆነ በተሻሻለው የቤተሰብ ሕግ በአንቀጽ 154 ላይ ተመልክቷል፡፡ ይህ ማለት ግን የልደት ምስክር ወረቀት ክርክር ሊነሳበት የማይችል ሙሉ እምነት ሊጣልበት የሚችል /Conclusive/ ማስረጃ ነው ማለት ግን አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 33440 ቅጽ 5[6]

[1] አመልካች አንበሳ የከተማ አውቶቡስ አገልግሎት ድርጅት እና ተጠሪዎች እነ ወ/ሮ ዘነበወርቅ ከበደ ህዳር 15 ቀን 2002 ዓ.ም.

[2] አመልካች የደ/ብ/ብ/ሕዝቦች ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፍትሕ ቢሮ እና ተጠሪአቶ አለማየሁ አስፋው መስከረም 30 ቀን 2007 ዓ.ም.

[3] አመልካች ዶ/ር ገነት ስዩም እና ተጠሪ እነ ቂርቆስ ክፍለ ከተማ ቀበሌ 17/18 አስተዳደር ጽ/ቤት /3 ሰዎች/   የካቲት 28 ቀን 2004 ዓ.ም.

[4] አመልካቾች እነ የወ/ሮ ጣይቱ ከበደ ወራሾች /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ ጥሩነሽ ኃይሌ /3 ሰዎች/ መጋቢት 11 ቀን 2004 ዓ.ም.

[5] አመልካች ወ/ሮ ዘነበች በያን እና ተጠሪ ወ/ት ብርቅነሽ ከበደ ታህሳስ 6 ቀን 2002 ዓ.ም.

[6] አመልካች ወ/ሮ ኪሮስ ገ/ማርያም እና ተጠሪ አቶ ግርማ ገብረስላሴ ሚያዝያ 21 ቀን 2000 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

Ethiopia secures release of 134 citizens from Oman prisons | Africanews

$
0
0

The Foreign Affairs Ministry said three flights carried the released prisoners to Ethiopia between October 1 and 5, local media FBC reported.

The inmates expressed gratitude to the Ethiopian Embassy in Oman for facilitating their return.

Details surrounding the release of the prisoners has not been disclosed.

In July, Ethiopia released 114 Somali prisoners from detention facilities and handed them over to the Somali government.

The release of the prisoners, who were returned to Mogadishu, followed talks between Somali Prime Minister Hassan Ali Khayre and his Ethiopian counterpart, Hailemariam Desalegn.

Their release was considered a sign of the good ties between the two countries.

Source: Ethiopia secures release of 134 citizens from Oman prisons | Africanews


Filed under: Legal news update

አፈ ጉባዔ፡ ስልጣንና ተግባር

$
0
0

በተወካዮች ምክር ቤት እና ፌዴሬሽን ምክር ቤት ሁለት ዋና እንዲሁም ሁለት ምክትል አፈ ጉባዔዎች በድምሩ አራት አፈጉባዔዎች ይገኛሉ፡፡ ምክትሎቹ እንደማንኛውም ምክትል ባለስልጣን ብዙም ትኩረት የሚስብ ስልጣን የላቸውም፡፡ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈጉባዔ ከምክር ቤቱ ጋር የተያያዙ በርካታ ስልጣንና ተግባራት ቢኖሩትም በንጽጽር ካየነው ከአራቱ አውራ ሆኖ የሚወጣው የተወካዮች ምክር ቤት አፈጉባዔ ነው፡፡ ለመሆኑ ስልጣንና ተግባራቱ ምንድናቸው?

ስለ ስልጣኑ ስፋትና ደረጃ ጠቅለል ያለ እይታ እንዲኖረን በተለያዩ ህጎች ለአፈጉባዔው የተሰጡ ስልጣንና ተግባራት በአጭሩ ከዚህ በታች ተዘርዝረዋል፡፡

ከዚያ በፊት ግን ስለ ስልጣኑ ደረጃ እና ስለ ህገ መንግስታዊ ሚናው ጥቂት ነጥቦች ማንሳት ያስፈልጋል፡፡ በአንድ አገር ውስጥ አፈጉባዔ ከፍተኛ ከሚባሉ የመንግስት ባለስልጣናት ረድፍ ይመደባል፡፡ ለምሳሌ በአሜሪካ ፕሬዚዳንቱ ከሞተ፤ ስልጣን ከለቀቀ ወይም በማናቸውም ምክንያት በፕሬዚዳንትነት መቀጠል ካልቻለ በስልጣን ሽግግሩ (presidential line of succession) ከምክትል ፕሬዚዳንቱ ቀጥሎ የሚገኘው አፈጉባዔው ነው፡፡

የዲሞክራሲ ባህል ባልዳበረበት እንደ ኢትዮጵያ ባለ አገር አፈጉባዔው ቁልፍ ሚና ይጫወታል፡፡ በፓርላማ ውስጥ ስልጣን ከጨበጠው ፓርቲ በተጨማሪ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ካሉ ይህ ሚናው በተጨባጭ ይታያል፡፡ የህዝብ ተወካዮች የመረጣቸውን ህዝብ ጥቅምና መብት የሚያስጠብቁት ፓርላማ ውስጥ በመናገር፤ በመወያየትና በመከራከር ብሎም ለቆሙለት ዓላማ ድምጻቸውን በመስጠት ነው፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ የአፈጉባዔው ተጽዕኖ ቀላል የሚባል አይደለም፡፡

በአፈጉባዔነት ለማገልገል የተለየ ክህሎትና ሙያ ወይም ችሎታ አይጠይቅም፡፡ ጥሩ የሚባል አፈጉባዔ ትልቁ መመዘኛው ገለልተኛ መሆን መቻሉ ላይ ነው፡፡ ለቦታው ታጭቶ ከተመረጠ በኋላ ዕውቀቱንና ጉልበቱን ማዋል ያለበት የወከለውን ፓርቲ ጥቅም በማስጠበቅ ሳይሆን ሁሉንም በህዝብ የተመረጡ ተወካዮች በማገልገል መሆን አለበት፡፡ በእንግሊዝ አፈጉባዔው ከተሾመበት ቀን ጀምሮ የፖለቲካ ፓርቲ አባልነቱን ማቋረጥ አለበት፡፡ ይህን ነጥብ አስመልክቶ በፓርላማው ድረ-ገፅ ላይ የሰፈረውን የሚከተለውን ጠቃሚ መረጃ ማየቱ ከአገራችን ሁኔታ ጋር ያለውን ልዩነት ለማነጻጸር ያህል ይረዳል፡፡

Speakers must be politically impartial. Therefore, on election the new Speaker must resign from their political party and remain separate from political issues even in retirement. However, the Speaker will deal with their constituents’ problems like a normal MP.

በአገራችን ይህ መሰረታዊ ነጥብ ብዙም ትኩረት አላገኘም፡፡ በዚህ የተነሳ አፈ ጉባዔው ስብሰባ በሚመራበት ወቅት ገለልተኛ፤ ፍትሀዊና ሚዛናዊ የሆነ መርህን መከተል እንዳለበት ከሚያሳስቡ ጥቂት ድንጋጌዎች[1] በስተቀር ገለልተኝነቱን የሚያረጋግጡ ህገ መንግስታዊ መርሆዎች ሆነ የህግ ማዕቀፎች የሉም፡፡

መብት፤ ጥቅምና ክብር

ከመብት ጥቅምና ክብር አንጻር የተወካዮች ም/ቤት አፈጉባዔ የሚኒስትር ማዕረግ ባላቸው ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎች ተርታ ይሰለፋል፡፡ ከስልጣናቱና መብቶቹ መካከል የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡፡

  • ከአፈ ጉባዔነቱ ሲነሳ ለከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎችን (ሚኒስትር፤ ሚኒስትር ዴኤታ እና ምክትል ሚኒስትር) መብትና ጥቅም ያገኛል፡፡[2] በምክር ቤት አባልነቱ ከሚያገኘው የመቋቋሚያ አበል፤ የስንብት ክፍያ እንዲሁም የመጓጓዣና የጓጓ ማንሻ አበል በተጨማሪ ሌሎች አባላት የማያገኙትን የመኖሪያ ቤት አበል፤ የተሸከርካሪ አበል፤ የሕክምና አገልግሎት፤ የግል ደህንነት ጥበቃ አገልግሎት እና በአፈ ጉባዔነት ሲሾም የመቋቋሚያ የሁለት ወር ደመወዝ ይሰጠዋል፡፡
  • የሪፐብሊኩን ሰንደቅ ዓላማ በተሸከርካሪ ላይ በመስቀል መጠቀም ይችላል፡፡ ይህ ልዩ መብት የተሰጣቸው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባዔ፤ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔና ምክትል አፈ ጉባዔ፤ የፌደራል መንግስቱ ሚኒስትሮች፤ የሀገሪቱ የጦር ሀይሎች ኤታማጆር ሹም፤ የፌደራል ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንቶችና የክልል መንግስታት ፕሬዚዳንቶች[3] ናቸው፡፡
  • የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በስራ ላይ በማይሆንበት ጊዜ ብሔራዊ የሃዘን ቀንና ሰንደቅ ዓላማ ዝቅ ብሎ የሚውለበለብባቸውን ሁኔታዎች ይወሰናል፡፡[4]

ጠቅላላ ስልጣናት

የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ህገ መንግስት የፌዴሬሽን ም/ቤት አፈ ጉባዔ ስልጣንና ተግባራት በአንቀጽ 66 ላይ በግልጽ ያስቀመጠ ቢሆንም የተወካዮች ም/ቤት አፈጉባዔውን ስልጣንና ተግባር በዝምታ አልፎታል፡፡ በአንቀጽ 58/4/ ምክር ቤቱ ዕረፍት ላይ በሚሆንበት ጊዜ ስብሰባ እንደሚጠራ ከማመልከት በስተቀር ስለ ስልጣኑ የሚናገር ድንጋጌ የለም፡፡ በአንቀጽ 66 የፌዴሬሽን ም/ቤት አፈጉባዔው የሚከተሉት ስልጣንና ተገባረት አሉት፡፡

  • የምክር ቤቱን ስብሰባዎች ይመራል፡፡
  • ምክር ቤቱን በመወከል ጠቅላላ የአስተዳደደር ስራዎች ይሰራል፡፡
  • ምክር ቤቱ በአባሎቹ የወሰነውን የዲሲፕሊን እርምጃ ያስፈጽማል፡፡

በህገ መንግስቱ በዝምታ ቢታለፍም የተወካዮች ም/ቤት አፈጉባዔ ከላይ የተዘረዘሩትን ጨምሮ ሌሎች ስልጣንና ተግባራት በኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአሰራርና የአባላት ስነ ምግባር ደንብ ቁ. 6/2008 ዓ.ም. አንቀጽ 9 ላይ ተሰጥቶታል፡፡ ከእነዚሀ መካከል በዋነኛነት የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡

  • ምክር ቤቱን በበላይነት ይመራል፡፡ ያስተዳድራል፡፡
  • የምክር ቤቱን ስብሰባዎች ይመራል፡፡ ስነ-ስርዓት ያስከብራል፡፡ ልዩና አስቸኳይ ስብሰባዎች ይጠራል፡፡
  • በስብሰባ ወቅት ለሚነሱ የትርጉም ጥያቄዎች ውሳኔ ይሰጣል ወይም ለሚመለከተው አካል ይመራል፡፡
  • የኮሚቴዎችን ሊቃነመናብርት፤ ምክትል ሊቃነመናብርት እና አባላት እንዲሁም ምክር ቤቱ በሕግ መሰረት በሚወከልባቸው አካላት ውስጥ የሚወከሉ አባላትን ያስመርጣል፡፡ እንዲወከሉ ያደርጋል፡፡
  • የቋሚ ኮሚቴዎችን ስራ ያስተባብራል፡፡
  • ምክር ቤቱን በመወከል ግንኙነት ያደርጋል፡፡

ከላይ በጥቅል አነጋገር የተጠቀሱት ስልጣናት በም/ቤቱ ደንብና ደንቡን ተከትሎ በወጡ ወደ 29 የሚጠጉ መመሪያዎች እንዲሁም ሌሎች ተዛማጅ ህጎች አንድ በአንድ ተዘርዝረዋል፡፡

የምክር ቤቱን ስብሰባ የመምራት ስልጣን

አፈ ጉባዔ በምክር ቤቱ በሚከናኑ ማናቸውም ተግባራት ላይ ሁሉ በቀጥታ ሆነ በተዘዋዋሪ እጁ አለበት፡፡ በጥያቄ[5] እና ሞሽን[6] አቀራረብ፤ በአጀንዳ አቀራረጽ፤[7] የውይይት ጊዜ አመዳደብ እና የተናጋሪ አመራረጥ፤[8] የስነ-ስርዓት ጥያቄ አቀራረብ፤[9] ድምጽ አሰጣጥ[10] እና ሌሎችም ጉዳዮች በአፈጉባዔው ተጽዕኖ ስር ናቸው፡፡

ለምሳሌ ስብሰባ በመምራት ስልጣኑ በሚከተሉት ምክንያቶች ስብሰባ ሊያቋርጥ ይችላል፡፡[11]

  • የስነ ስርዓት ወይም የስነ ምግባር ጉድለት የዕለቱን ስብሰባ ሂደት በጎላ መልኩ የሚያውክ መሆኑን ከተገነዘበ
  • በስነ ስርዓት ወይም በስነ ምግባር ጉድለት ምክንያት የፀጥታ መደፍረስ የተፈጠረ ከሆነ ወይም ሊፈጠር ይችላል ብሎ ካመነ/ከገመተ
  • የስነ ስርዓት ወይም የስነ ምግባር ጉድለቱ በአባላት መካከል ጠብ ሊያስነሳ የሚችል መሆኑን ከተገነዘበ
  • የመናገር ዕድል ሳይሰጠው እንደተሰጠው በመቁጠር ንግግር የጀመረ አባል በሚኖርበት ጊዜ አፈጉባዔው ንግግሩን አስቁሞ ለተፈቀደለት አባል ይሰጣል፡፡[12]
  • በአጀንዳነት የቀረበ ጉዳይ በተያዘለት ጊዜ ውስጥ በቂ ውይይት ከተደረገበት በኋላ ወይም አፈጉባዔው በቂ ውይይት ተደርጓል ብሎ ሲያምን ድምጽ እንዲሰጥበት ያደርጋል፡፡[13]

የምክር ቤቱን አሰራር የሚመለከት ሞሽን ማለትም ምክር ቤቱ የሚወያይበትን አጀንዳ ወይም ሂደት በተመለከተ የሚቀርብ የስነ ስርዓት ጥያቄ ውሳኔ የሚያገኘው በአፈጉባዔው ነው፡፡[14] የስነ ስርዓት ጥያቄን በሚመለከት ምክር ቤቱ በ2000 ዓ.ም. ባወጣው መመሪያ[15] ላይ በዝርዝር የተቀመጠ ሲሆን በመመሪያው መሰረት አፈጉባዔው የሚከተሉት ስልጣናት አሉት፡፡

  • ለጥያቄ አቅራቢው ዕድል የመስጠት
  • ጥያቄው የስነ ስርዓት ጥያቄ መሆን ወይም አለመሆኑን የመወሰን
  • አለአግባብ የቀረበን የስነ ስርዓት ጥያቄን የማስቆም

አፈጉባዔው በስነ ስርዓት ጥያቄ ላይ የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ ሲሆን ውሳኔ በሰጠበት ጥያቄ ላይ ድጋሚ ጥያቄ ሊቀርብ አይችልም፡፡ በስነ ስርዓት ጥያቄ ላይ ሆነ ሌሎች በእርሱ ስልጣን ስር በሚወድቁ ጉዳዮች ላይ አፈጉባዔው ውሳኔ በሚሰጥበት ወቅት፤

  • በማንኛውም አባል ተቃውሞ፤ ጥያቄ፤ በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ ትችት ሊቀርብበት አይችልም፡፡
  • ማንኛውም አባል ትርጉም ሊሰጠው ወይም እንዲተረጎም ሊጠይቅ አይችልም፡፡
  • ምክንያት ሊቀርብበት ወይም አፈጉባዔው ምክንያት እንዲያቀርብበት ሊጠየቅ አይችልም፡፡
  • በሚመለከተው ማንኛውም ሰው ተግባራዊ መደረግ አለበት፡፡

በእርግጥ ማንኛውም አባል መሰረታዊ ሞሽን ካቀረበ ከላይ በተዘረዘሩት ነጥቦች ላይ ምክር ቤቱ ሊወያየበት ይችላል፡፡ ይሁን እንጂ የሞሽን አቀራረብ ስርዓቱ በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ የአፈጉባዔውን ይሁንታ ማግኘት አለበት፡፡ ማንኛውም ሞሽን የሚቀርበው በምክር ቤት ጉዳዮች አማካሪ ኮሚቴ ወይም በአፈጉባዔው ሲፈቀድ ነው፡፡[16] አፈጉባዔው የዚህ ኮሚቴ ሰብሳቢ እንደመሆኑ ከላይ በተዘረዘሩት ነጥቦች ላይ እርሱ ካልፈቀደ በስተቀር በምክር ቤቱ የሚታይበት አጋጣሚ የለም፡፡

ይግባኝ ሰሚ

  • ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን እና የህዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም የመምሪያ ኃላፊዎች ላይ የሚተላለፍ አስተዳደራዊ ውሳኔ ላይ ይግባኝ ይሰማል፡፡[17]
  • በምክር ቤቱ አባላት ላይ የመብት መጣስ ተግባር ሲፈጸም ጉዳዩ አብዛኛውን አባል የሚመለከት ካልሆነ በስተቀር አቤቱታ የሚቀርበው ለህግ፤ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ነው፡፡ ኮሚቴው አቤቱታውን አጣርቶ ለአፈጉባዔው የውሳኔ ሀሳብ ያቀርባል፡፡ አፈጉባዔው ደግሞ የራሱን ውሳኔ ይሰጣል፡፡[18]

ዕጩ አቅራቢና ሿሚ

  • የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነርና ምክትል ኮሚሽነር ዕጩዎችን እንዲሁም ዋና ዕንባ ጠባቂ፤ ምክትክ ዋና ዕንባ ጠባቂና ሌሎች ዕንባ ጠባቂዎችን የሚመለምለው የዕጩ አቅራቢ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነው[19]፡፡
  • የፌደራል ዋና ኦዲተር እና ምክትል ዋና ኦዲተሮች ቦታ በተመሳሳይ ጊዜ ክፍት የሆነ እንደሆነ የኦዲት ዳይሬክተሮችን ለሶስት ወራት ጊዜ መድቦ ሊያሰራ ይችላል፡፡[20]
  • ከመንግስት ዋና ተጠሪና ከዋና ተቃዋሚ ፓርቲ ዋና ተጠሪ ጋር በመመካከር የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጽህፈት ቤት ዋና ፀሀፊ ይመድባል፡፡ ምክትል ፀሀፊውንና ሌሎች የመምሪያ ሀላፊዎችን ደግሞ በዋና ፀሀፊው አቅራቢነት ብቻውን (መመካከር ሳያስፈልገው) ይሾማል፡፡[21] ዋናው፤ ምክትሉና የመምሪያ ሀላፊዎች በፌደራል የመንግስት ሰራተኞች ህግ ተፈጻሚ አይሆንባቸውም፡፡ የስራ ሁኔታቸው የሚወሰነው አፈ ጉባዔው ብቻውን በሚያወጣው መመሪያ ነው፡፡[22]

አባል እና ሰብሳቢ

  • የሀገር አቀፍ የኤች.አይ.ቪ/ኤድስ መከላከያና መቆጣጠሪያ ምክር ቤት አባል ነው፡፡[23]
  • በምክር ቤቱ የኮሚቴዎች አደረጃት መሰረት ስድስት ዓይነት ኮሚቴዎች ተዋቅረዋል፡፡ እነዚህም፤ የምክር ቤት ጉዳዮች አማካሪ ኮሚቴ፤ አስተባባሪ ኮሚቴ፤ ልዩ ኮሚቴ፤ ቋሚ ኮሚቴ፤ ንዑስ ኮሚቴ፤ ጊዜያዊ ኮሚቴ ናቸው፡፡ በልዩ ኮሚቴነት የተዋቀረው የመከላከያና የብሔራዊ መረጃ ደህንነት ጉዳዮች ልዩ ኮሚቴ ብቻ ሲሆን በቋሚ ኮሚቴ ስር 18 ኮሚቴዎች ይገኛሉ፡፡ ከስድስቱ የኮሚቴ ዓይነቶች መካከል ጠንካራ የሚባሉት የሶስቱ ማለትም የምክር ቤት ጉዳዮች አማካሪ ኮሚቴ፤ የመከላከያና የብሔራዊ መረጃ ደህንነት ጉዳዮች ልዩ ኮሚቴ እና የአስተባባሪ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነው፡፡[24]
  • በምክር ቤቱ ውስጥ ሴቶችን የሚመለከቱ ሁለት ኮሚቴዎች ይገኛሉ፡፡ አንደኛው የሴቶችና ህጻናት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የሴቶች ኮከስ ተብሎ የሚጠራ ቡድን ነው፡፡ ይህ አካል ዋነኛ ትኩረቱ በሴት አባላት ልምድ ልውውጥ እንዲሁም የሴቶችን መብትና ተጠቃሚነት የሚመለከቱ አጀንዳዎች ምክክር ማካሄድ ላይ ነው፡፡ ይህ ኮከስ ተጠሪነቱ ለአፈ ጉባዔው ነው፡፡

የዲሲፕሊን እርምጃ

የንግግር ስነ ስርዓት ወይም ስነ ምግባር የጣሰ አባል ንግግር ያስቆማል፡፡ አባሉን በስም ጠቅሶ የእርምት ማሳሰቢያ ይሰጣል፡፡ ማሳሰቢያውን የማያከብር ከሆነ ወይም ከስነ ስርዓት ወይም ከስነ ምግባር ውጭ የሆነ ባህሪ አሳይቷል ብሎ ካመነ ከስብሰባ እንዲወጣ ሊያዝ ይችላል፡፡ ከዚያም አልፎ እንደሁኔታው እስከ ሁለት ተከታታይ የስብሰባ ቀናት በአፈጉባዔው ሊታገድ ይችላል፡፡[25]

ሕግ ማውጣትና መተርጎም

  • በምክር ቤቱ የፀደቀ ህግ ፕሬዚዳንቱ በ15 ቀናት ውስጥ ካልፈረመበት በአፈ ጉባዔው ስምና ፊርማ ወጥቶ ስራ ላይ ይውላል፡፡ ህጉ በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከመውጣቱ በፊት የቴክኒክ እርምት ማድረግ አስፈላጊ ሆኖ ካገኘው ብቻውን እርምት ያደርጋል፡፡[26]
  • አዋጅ ቁ. 906/2007 ‘ን’ (የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጽህፈት ቤትን እንደገና ለማቋቋም የወጣው አዋጅ) ለማስፈጸም ብቻውን መመሪያ የማውጣት ስልጣን ተሰጥቶታል፡:[27]
  • ምክር ቤቱ የሚያወጣው የአሠራርና የስነ ምግባር ደንብ ለማስፈጸም የሚረዱ መመሪያዎችን ለማውጣት ስልጣን የተሰጠው ለምክር ቤት ጉዳዮች አማካሪ ኮሚቴ ሲሆን አፈጉባዔው የዚህ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነው፡፡
  • በህግ ተርጓሚነት ሚናው በስብሰባ ወቅት የደንብ ቁ. 6/2008 ይዘትን አስመልክቶ የትርጉም ጥያቄ ከተነሳ ደንቡን የመተርጎም ስልጣን አለው፡፡

በጀት

በረቂቅ በጀት የመገምገምና የውሳኔ ሀሳብ የማቅረብ ሂደት ላይ የአፈ ጉባዔው ሚና ጎልቶ ይወጣል፡፡ አስራ ስምንቱም ቋሚ ኮሚቴዎች በተቋቋሙበት ዘርፍ ያከናወኑትን ተግባር በተመለከተ ሪፖርት ወይም የውሳኔ ሀሳብ ወይም ውሳኔ የሚያቀርቡት በዋናነኛነት ለአፈ ጉባዔው ወይም በቀጥታ ለምክር ቤቱ ሲሆን የሁሉም ተጠሪነት ለምክር ቤቱ ነው፡፡ አፈጉባዔው ከቋሚ ኮሚቴ የቀረበለትን ሪፖርት፤ የውሳኔ ሀሳብ ሆነ ውሳኔ እንደገና የመከለስና የማስተካከል ስልጣን የለውም፡፡ ሆኖም ረቂቅ በጀትን በተመለከተ አሰራሩ የተለየ አካሄድ ይከተላል፡፡

የበጀትና ፋይናንስ ቋሚ ኮሚቴ በተለያየ ሂደት ያለፈውን የመጨረሻውን ረቂቅ በጀት ከመረመረ በኋላ አስተያየቱን ወይም የውሳኔ ሀሳቡን በቀጥታ ለምክር ቤቱ አያቀርብም፡፡ ከዚያ ይልቅ አስተያየቱን በአፈ ጉባዔው በኩል ለምክር ቤት ጉዳዮች አማካሪ ኮሚቴ ይልካል፡፡ ኮሚቴው የተላከለትን አስተያየት እንደገና በመመርመር የራሱን የውሳኔ ሀሳብ ለምክር ቤት ያቀርባል፡፡[28] የዚህ ኮሚቴ ዋና ሰብሳቢ ደግሞ አፈጉባዔው ነው፡፡

[1] የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የምክር ቤቱ የክርክርና የውይይት ስነ ስርዓት መመሪያ ቁ. 16/2001 ዓ.ም. አንቀጽ 25/2/ ሀ

[2]አዋጅ ቁ. 653/2001 ከሀላፊነት የተነሱ የሀገርና የመንግስት መሪዎች፤ ከፍተኛ የመንግስት ሀላፊዎች፤ የምክር ቤት አባላትና ዳኞች መብቶችና ጥቅሞች አዋጅ በተጨማሪም አዋጅ ቁ. 934/2008 ከሀላፊነት የተነሱ የሀገርና የመንግስት መሪዎች፤ ከፍተኛ የመንግስት ሀላፊዎች፤ የምክር ቤት አባላትና ዳኞች የሚያገኟቸውን መብቶችና ጥቅሞች መወሰኛ /ማሻሻያ/ አዋጅ ይመለከቷል፡፡

[3] አዋጅ ቁ. 654/2001 የሰንደቅ ዓላማ አዋጅ አንቀጽ 21/3/

[4] አዋጅ ቁ. 863/2006 የሰንደቅ ዓላማ /ማሻሻያ/ አዋጅ አንቀጽ 2/2/

[5] የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስለ ጥያቄ አቀራረብ የወጣ መመሪያ ቁ. 2/2000 ዓ.ም.

[6] የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስለ ሞሽን አቀራረብ የወጣ መመሪያ ቁ. 3/2000 ዓ.ም. እንዲሁም ስለ ማሻሻያ ሞሽን አቀራረብ የወጣ መመሪያ ቁ. 4/2000 ዓ.ም.

[7] የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአጀንዳ አቀራረፅ የሚመራበትን አሠራር ለመወሰን የወጣ መመሪያ ቁ. 5/2000 ዓ.ም. እና የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በዕለታዊ አጀንዳ ያልተቀረፀ ጉዳይ በምክር ቤቱ እንዲታይ ሞሽን ስለማቅረብ የወጣ መመሪያ ቁ. 8/2000 ዓ.ም.

[8] የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውይይት ጊዜ አመዳደብ እና የተናጋሪ አመራረጥ የሚመራበትን አሠራር ለመወሰን የወጣ መመሪያ ቁ. 6/2000 ዓ.ም.

[9] የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የስነ ስርዓት የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የስነ-ስርዓት ጥያቄ አቀራረብን ለመወሰን የወጣ መመሪያ ቁጥር 7/2000

[10] የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የድምጽ አሰጣጥ መመሪያ ቁ. 9/2000 ዓ.ም.

[11] መመሪያ ቁ. 16/2001 ዓ.ም. አንቀጽ 47/1/

[12] ደንብ ቁ. 6/2008 አንቀጽ 29/4/)

[13] መመሪያ ቁ. 9/2000 ዓ.ም. አንቀጽ 12/1/

[14] ደንብ ቁ. 6/2008 አንቀጽ 44/1/

[15] መመሪያ ቁጥር 7/2000 ዓ.ም. አንቀጽ 10

[16] ደንብ ቁ. 6/2008 አንቀጽ 39/2/

[17] አዋጅ ቁ. 210/1992 እና አዋጅ ቁ. 211/1992 የሁለቱም አንቀጽ 32

[18] ደንብ ቁ. 6/2008 አንቀጽ 142/1/ /3/ እና /4/

[19] አዋጅ ቁ. 210/1992 የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ እና አዋጅ ቁ. 211/1992 የህዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም ማቋቋሚያ አዋጅ የሁለቱም አንቀጽ 11

[20] አዋጅ ቁ. 982/2008 የፌደራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ማቋቋሚያ አዋጅን  ለማሻሻል የወጣ አዋጅ አንቀጽ 12/3/

[21] አዋጅ ቁ. 906/2007 የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጽህፈት ቤትን እንደገና ለማቋቋም የወጣ አዋጅ አንቀጽ 6/1/ ሀ እና ለ

[22] አዋጅ ቁ. 906/2007 አንቀጽ 6/3/

[23] አዋጅ ቁ. 276/1994 ሀገር አቀፍ የኤች.አይ.ቪ/ኤድስ መከላከያና መቆጣጠሪያ ምክር ቤት እና የኤች.አይ.ቪ/ኤድስ መከላከያና መቆጣጠሪያ ጽሕፈት ቤት ማቋቋሚያ አዋጅ አንቀጽ 4/3/

[24] ደንብ ቁ. 6/2008 ዓ.ም. አንቀጽ 152፤ 155 እና 160

[25] የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የስነ ምግባር መመሪያ ቁ. 24/2001 ዓ.ም. አንቀጽ 21/1-5/

[26] ደንብ ቁ. 6/2008 ዓ.ም. አንቀጽ 58

[27] አዋጅ ቁ. 906/2007 አንቀጽ 11

[28] የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የበጀት አፀዳደቅ ሂደትን ለመወሰን የወጣ መመሪያ ቁጥር 10/2000 ዓ.ም. አንቀጽ 10/1/ እንዲሁም የምክር ቤቱን በጀት በተመለከተ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአሰራርና የአባላት የሥነ-ምግባር ደንብ ቁ.6/2008 ዓ.ም. አንቀጽ 214


Filed under: Articles

የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የአጣሪ ዳኝነት (judicial review) ስልጣን

$
0
0

የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሰበር ስልጣን በቀጥታ ከህገ መንግስቱ ይመነጫል፡፡ ሆኖም የስልጣኑን ወሰን የሚያሰምረው የህገ መንግስቱ አንቀጽ 80/3/ ሀ የአማርኛውና እንግሊዝኛው ቅጂ ግልጽ መፋለስ ይታይበታል፡፡ በአማርኛው ንባብ የሰበር ችሎት መሰረታዊ ‘የህግ ስህተት ያለበትን ማናቸውንም የመጨረሻ ውሳኔ’ የማረም ስልጣን ይኖረዋል፡፡ (ሰረዝ የተጨመረ) የእንግሊዝኛው ቅጂ ደግሞ over any final court decision የሚል አገላላጽ በመጠቀም ስልጣኑን ፍርድ ቤት የመጨረሻ ውሳኔ በሰጠባቸው ጉዳዮች ላይ ብቻ ይገድበዋል፡፡

የድንጋጌውን ይዘት ዝርዝር የሚወስነው ህግ ከእንግሊዝኛው ቅጂ ጋር ይስማማል፡፡ በፌደራል ፍርድ ቤቶች አዋጅ ቁ. 25/1988 አንቀጽ 10 የፌ/ጠ/ፍ/ቤት የሰበር ስልጣን የሚያገኝባቸው ሶስት ጉዳዮች ተዘርዝረዋል፡፡ እነዚህም፤

  • የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በይግባኝ አይቶ የመጨረሻ ውሳኔ የሰጠባቸው ጉዳዮች
  • የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት መደበኛ ችሎት የመጨረሻ ውሳኔ የሰጠባቸው ጉዳዮች
  • የክልል ጠቅላይ ፍ/ቤት መደበኛ ችሎት በይግባኝ አይቶ የመጨረሻ ውሳኔ የሰጠባቸው ጉዳዮች

በሶስቱም ጉዳዮች በውሳኔ ሰጭነት የተጠቀሱት ተቋማት መደበኛ ፍርድ ቤቶች ብቻ ናቸው፡፡ በኢ.ፌ.ዲ.ረ ህገ መንግስት አንቀጽ 80/3/ ሀ የእንግሊዝኛው ቅጂ ላይ court የሚለው ቃል እንዲሁ ይህንኑ ሀሳብ ያንጸባርቃል፡፡ ሆኖም የአማርኛው ንባብ ውሳኔ ሰጭውን በዝምታ አልፎታል፡፡ ላይ ላዩን ሲታይ ዝምታው ለህገ መንግስታዊ ትርጉም በር የከፈተ አይመስልም፡፡ ‘የመጨረሻ ውሳኔ’ የሚለው አገላለጽ ፍርድ ቤትን ታሳቢ አድርጓል ቢባል ብዙዎችን ያስማማል፡፡

ሆኖም ችግሩ ከቋንቋ አጠቃቀም ያልዘለለ የሚመስለው የአንቀጽ 80/3/ ሀ ድንጋጌ በተግባር ህገ መንግስታዊ ጥያቄ አስነስቶ የሰበር ችሎትን የአጣሪ ዳኝነት ስልጣን አስፍቶታል፡፡ በሰ/መ/ቁ. 43511[1] ከአዋጅ ውጪ የተወረሱ ንብረቶችን በተመለከተ ከፊል ዳኝነታዊ ስልጣን የተሰጠው የፕራይቬይታይዜሽን ኤጀንሲ ቦርድ ያስተላለፈው ውሳኔ በቀጥታ በሰበር እንዲታይ አቤቱታ ቢቀርብም አጣሪ ችሎቱ ጉዳዩ አስተዳደራዊ መሆኑን በመጠቆም ውድቅ አድርጎታል፡፡ ሆኖም በመዝገቡ ላይ አመልካች ሆነው የቀረቡት አቤቱታ አቅራቢዎች የውሳኔውን ህገ መንግስታዊነት በመሞገት ለህገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ አቤቱታ አስገቡ፡፡ አጣሪውም ለጥያቄያቸው አዎንታዊ ምላሽ ባለመስጠቱ የመጨረሻ አማራጫቸውን በመጠቀም ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አመለከቱ፡፡ ም/ቤቱ የችሎቱን ስልጣን በማረጋገጥ መዝገቡን ወደ ሰበር ችሎት መለሰው፡፡ የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የቦርዱን ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት የማረም ስልጣን እንዳለው በማረጋገጥ የተሰጠው ይህ የም/ቤቱ ውሳኔ ‘የመጨረሻ ውሳኔ’ በሚል በህገ መንግስቱ አንቀጽ 80/3/ ሀ ላይ የተቀመጠውን አገላለጽ ከእንግሊዝኛ ቅጂ ፍጹም የተለየ ይዘትና መልዕክት ሰጥቶታል፡፡ በውጤቱም ከፍርድ ቤት ውጭ ያሉ ከፊል የዳኝነት አካላት ላይ የሰበር ችሎት የአጣሪ ዳኝነት ስልጣን እንዳለው አረጋግጧል፡፡

የም/ቤቱ ውሳኔ ህገ መንግስታዊ ፋይዳው ስር ነቀልና መሰረታዊ ነው፡፡ የስር ፍ/ቤቶችን የህግ ስህተት በማረም ብቻ ተወስኖ የነበረው የሰበር ችሎት በም/ቤቱ ‘በተጨመረለት’ ስልጣን ከፊል ዳኝነታዊ ስልጣን የተሰጣቸው የአስተዳደር አካለት የሚያስተላልፉትን ውሳኔ ጭምር የማረም የአጣሪ ዳኝነት ስልጣን ይኖረዋል፡፡ ችሎቱም ዳኝነታዊ የአስተዳደር ውሳኔዎችን ማረም ህገ መንግስታዊ ሚናው እንደሆነ በሌሎች ሁለት መዝገቦች በሰጣቸው ውሳኔዎች በተግባር አረጋግጧል፡፡

በሰ/መ/ቁ. 92546[2] የድሮው ፍትሕ ሚኒስቴር የአሁኑ ጠቅላይ ዓቃቤ ህግ የዲሲፕሊን ውሳኔ በቀጥታ ለሰበር ችሎት ቀርቦ ተሸሯል፡፡ አቤቱታ አቅራቢው በሚኒስትሩ የዲሲፕሊን እርምጃ የተወሰደበት ዓቃቤ ህግ ሲሆን ጉዳዩ በሰበር ችሎት ከመስተናገዱ በፊት በሌላ ፍርድ ቤት አልታየም፡፡ በመዝገቡ ላይ በችሎት የዳኝነት ስልጣን አከራካሪ ጭብጥ ሆኖ ባይወጣም የህገ መንግስቱ አንቀጽ 80/3/ ሀ እና አዋጅ ቁ፣ 25/88 አንቀጽ 10 ተጠቅሶ የቀረበውን አቤቱታ ችሎቱ መቀበሉ ሲታይ የአጣሪ ዳኝነት ስልጣኑ ጠንካራ መሰረት እየያዘ እንደመጣ እንደሆነ አስረጂ ነው፡፡ በሰ/መ/ቁ. 61221 ቅጽ 14[3] የተያዘው አቋም ይህንን ሀሳብ ያጠናክራል፡፡ በዚህ መዝገብ በሰፈረው ህግ ትርጉም በፍርድ ቤት እንዳይታዩ በመጨረሻ ማሰሪያ አንቀጽ (finality clause) ገደብ የተደረገባቸው ውሳኔዎች ሳይቀር በችሎቱ የአጣሪ ዳኝነት ስር እንዲወድቁ ተደርገዋል፡፡ ጉዳዩ የታየው አዋጅ ቁ. 714/2003 እና 715/2003 ከመውጣታቸው በፊት ሲሆን ቀድሞ በነበሩት የጡረታ ህጎች የማህበራዊ ዋስትና ጉባኤ ውሳኔ የመጨረሻ በመሆኑ በይግባኝ ሆነ በቀጥታ ክስ በመደበኛ ፍ/ቤቶች ሊታይ አይችልም፡፡

በሰ/መ/ቁ. 61221 የሰበር አቤቱታ የቀረበው የጉባዔውን የመጨረሻ ውሳኔ በመቃወም ነው፡፡ ሆኖም በችሎቱ የዳኝነት ስልጣን ላይ በተጠሪ በኩል ተቃውሞ በመቅረቡ የስልጣን ምንጭ አከራካሪ ጭብጥ ሆኖ ወጥቷል፡፡ ይህንን በማስመልከት ህገ መንግስቱን እና አዋጅ ቁ. 25/88 በማጣቀስ የሚከተለው የህግ ትርጉም ተሰጥቷል፡፡

ጉዳዩ በተነሳበት ጊዜ ስራ ላይ በነበረው ሕግ አግባብ ማህበራዊ ዋስትና ይግባኝ ሰሚ ጉባኤ የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ ነው ከተባለ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ መንግስት አንቀጽ 80(3(ሀ)) እና አዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀጽ 10 በተመለከተው አግባብ ለዚህ ሰበር ችሎት አቤቱታ ከማቅረብ የሚከለክል ሕጋዊ አግባብ የለም፡፡

 

[1] አመልካች የሟች አቶ ዋሲሁን መኮንን ሚስትና ወራሾች /8 ሰዎች/ እና ተጠሪ የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ ሰ/መ/ቁ. 43522 ቅጽ 14 ጥቅምት 23 ቀን 2005 ዓ.ም.

[2] አመልካች አቶ አብዱራዛቅ ኢብራሒም እና ተጠሪ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር ሰ/መ/ቁ. 92546 ቅጽ 15 ታህሳስ 18 ቀን 2006 ዓ.ም.

[3] አመልካች አቶ አከለ ምህረቱ እና ተጠሪ ማህበራዊ ዋስትና ኤጀንሲ መስከረም 22 ቀን 2005 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

የክስ ምክንያት- የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0
  1. አንድ ሰው አንድን ነገር ከአንድ ሰው ላይ ለማግኘት ፍ/ቤቱ እንዲወስንለት ክስ ለማቅረብና ዳኝነት ለማግኘት የሚያስችለው የፍሬ ነገር ሁኔታ

ማንም ሰው በህግ ችሎታ ኖሮት በሌላ ሰው ላይ ማናቸውንም ክስ ለማቅረብ እንዲችል አስቀድሞ ለክሱ መነሻ በሆነው ነገር ወይም ክሱ በተመሠረተበት ነገር ላይ ጥቅም ወይም መብት ያለው መሆኑ መረጋገጥ እንደሚገባው የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ. 33 ይደነግጋል፡፡ በዚህም ከሣሽ ከተከሣሽ ላይ ሊፈፀም የሚችል መብት አለኝ ብሎ ለማለት አስቀድሞ ለመብቱ መገኘት መነሻ የሆነውን ነገር በማረጋገጥ የተጠየቀውን ዳኝነት ለማግኘት ከሣሹ በሕግ መብት ያለው መሆን ይኖርበታል፡፡

የክስ ምክንያት አለ ብሎ ለመወሰን የሚቻለው በክሱ ላይ የቀረበው ነገር ቢረጋገጥ ከሣሹ የጠየቀውን ዳኝነት ለማግኘት ሕግ ይፈቅድለታል ወይ? ለሚለው ጥያቄ አዎንታዊ ምላሽ መስጠት ሲቻል ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 16273 ቅጽ 2፣[1] ስለ አሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ የወጣ አዋጅ ቁ. 42/85 አንቀጽ 9፣ ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 29፣ 80/2/፣ 224/2/፣ 23/1/ ሀ ፣ 224/2/፣ 23/1//ሀ/፣ 33፣ ሮበርት አለን ሴድለር በችሎቱ እንደተጠቀሰ

ሻጭ ከሽያጭ ውሉ በሚመነጭ ግዴታ የተሸጠውን ነገር ስመ ሀብትነት በሚመለከተው ክፍል ቀርቦ ለማዛወር እንደገባው ግዴታ ይፈጽምልኝ የሚል ክስ የክስ ምክንያት አለው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 82234 ቅጽ 15 [2]

አንድ ክስ ሊቀርብ የሚገባው የክስ ምክንያት ሲኖረው ሲሆን የክስ ምክንያትም ተከሣሽ ለከሣሽ ሊፈጽመው የሚገባው ግዴታ መኖሩ ጋር ተያይዞ ሊነሣ የሚችለውን ጥያቄ አዎንታዊ ምላሽ መስጠት የሚቻልበት ሁኔታ ስለመኖሩ ሲረጋገጥ የሚታወቅ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 33945 ቅጽ 12፣[3] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 231(1) ሀ

  1. ክስ ለማቅረብ የሚያስችል መነሻ ምክንያት

በፍ/ብ/ሕ/ሥ/ሥ/ቁ. 231 ላይ እንደተመለከተው ማንኛውም ፍርድ ቤት የክስ አቤቱታ ሲቀርብለት ተከሣሽ የሆነው ወገን ክሱን እንዲከላከል ከመጥራቱ በፊት ከሳሽ ክሱን ለማቅረብ የሚያስችል መነሻ ምክንያት ያለው ስለመሆኑና ፍ/ቤቱም አቤቱታውን ተቀብሎ ለማየት ስልጣን ያለው ስለመሆኑ መመርመር ይኖርበታል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 32147 ቅጽ 6፣[4] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ 231

አንድ ሰው በተለያዩ ምክንያቶች በአባቱ ብቻ ሳይሆን በአሳዳጊው ስም ጭምር ሊጠራ የሚችልባቸው አጋጣሚዎች መኖራቸው የሚታወቅ ሲሆን እንዲህ ዓይነቱ ሰው ተገቢ ሆኖ ባገኘው ጊዜ በአሳዳጊው ስም ጭምር መጠራቱ ቀሪ ሆኖ በፍትሐብሔር ሕጉ መሰረት በአባቱ ስም ብቻ እንዲጠራ የመወሰን መብት ያለው በመሆኑ ይህንኑ መብቱን በፍርድ ለማረጋገጥ የሚያቀርበው የዳኝነት ጥያቄ የክስ ምክንያት የለውም የሚባልበት ሕጋዊ ምክንያት አይኖርም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 95995 ቅጽ 15[5]

ከባዶ ቦታ ሽያጭ የመነጨ ግዴታ ለማስፈጸም የሚቀርብ አቤቱታ የክስ ምክንያት የለውም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 27739 ቅጽ 6[6]

[1] አመልካች የኢት/ ቴሌኮሙኒኬሽን ኮርፖሬሽን እና ተጠሪ አቶ ገንታ ገምአ ጥቅምት 22 ቀን 1998 ዓ.ም. በተጨማሪ አመልካች አቶ ደጀኔ በላቸው እና ተጠሪ አቶ ነስሩ አወል ሰኔ 17 ቀን 2002 ዓ.ም. ሰ/መ/ቁ. 45247 ቅጽ 9 ይመለከቷል፡፡

[2] አመልካች አቶ አየለ መኮንን እና ተጠሪዎች እነ ወ/ሮ ጦቢያው ወንድም ገዛው /6 ሰዎች/ የካቲት 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

[3] አመልካች አቶ ሣልህ ሁሴን እና ተጠሪ ደግፌ ደርቤ ጥቅምት 20 ቀን 2001 ዓ.ም.

[4] አመልካች አቶ መሐመድ አብዲ እና ተጠሪ አቶ አብዱረህማን አብዲ መጋቢት 9 ቀን 2000 ዓ.ም.

[5] አመልካች ወ/ት ሞሚና ሡልጣን ኮርዋላ እና ተጠሪ የለም የካቲት 10 ቀን 2006 ዓ.ም.

[6] አመልካች አቶ ድንቁ ገላው ተጠሪ ወ/ሮ ዋለ እሸቴ ጥቅምት 28 ቀን 2000 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

ህጋዊነትና ካርታ ማምከን

$
0
0

ከጥቂት ዓመታት ወዲህ የባለቤትነት ማረጋገጫ የመስጠት ስልጣን ያላቸው አካላት ‘ካርታ ማምከን’ የሚሉት አዲስ ፈሊጥ አምጥተዋል፡፡ ፍርድ ቤቶችም ቃሉን በተውሶ እያዘወተሩት ወደ ህግ ቃል እየቀየሩት ነው፡፡ ይህ የማምከን እርምጃ እስከ 2005 ዓ.ም. ድረስ በተደጋገሚ ሲስተዋል የነበረ አሳዛኝ ክስተት ነው፡፡ ህገ መንግስታዊ ንብረት የማፍራት መብትን አደጋ ውስጥ የከተተው ‘ከመሬት ተነስቶ’ ካርታ የማምከን ተግባር በቅርብ ሆኖ የሚቆጣጠረው በመጥፋቱ የተነሳ አስተዳደሩ ከህገ ወጥነት ወደ ጋጠ ወጥነት ተሸጋግሯል፡፡ በአስረጂነት ከሚጠቀሱ የሰበር ችሎት መዝገቦች መካከል የሰ/መ/ቁ 17712 አንደኛው ነው፡፡ በዚህ መዝገብ አመልካች ሆኖ የቀረበው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጽ/ቤት ሲሆን ተጠሪ የወሮ ሳድያ እስማኤል ወራሾች ናቸው፡፡ የጉዳዩ አመጣጥና በሰበር የተሰጠው ውሳኔ በአጭሩ እንዲህ ይተረካል፡፡

ክርክሩ የተጀመረው በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ሲሆን ተጠሪዎች በውርስ የተላለፉላቸው በአዲስ አበባ የሚገኙ ሁለት የንግድ ቤቶችን ተከራይተው የሚሰሩባቸው ግለሰብ ቤቶቹን እንዲያስረክቧቸውና ያልተከፈለ ኪራይም እንዲከፍሉ በማለት ክስ ያቀርባሉ፡፡ ፍርድ ቤቱም መብታቸውን በማረጋገጥ ወሰነላቸው፡፡ ከውሳኔ በኋላ የአዲስ አበባ መስተዳደር ቤቶቹ በአዋጅ ቁጥር 47/67 የተወረሱና ከዚህ ቀደም ተሰጥቶ የነበረው የባለቤትነት ደብተር በአዲስ አበባ አስተዳደር ሥራና ከተማ ልማት ቢሮ የቤቶች ጉዳይ መምሪያ የተሰረዘ መሆኑን በመግለፅ በክርክሩ ውስጥ በተቃውሞ ገብቶ የባለቤትነት ጥያቄ ያነሳል፡፡

ጉዳዩን በመጀመሪያ ደረጃ እና በይግባኝ ያዩት የስር ፍ/ቤቶች ‘ቤቶቹ ስለመወረሳቸው የሚያረጋግጥ የመረካከቢያ ቅፅ አልቀረበም’ በሚል የአስተዳደሩን ጥያቄ ውድቅ አደረጉት፡፡ አስተዳደሩ የሥር ፍርድ ውሳኔዎች መሠረታዊ የሕግ ስህተት ስላለባቸው ይታረምልኝ በማለት የሰበር አቤቱታ በማቅረቡ የሰበር ችሎት የሚከተለውን ውሳኔ በድምፅ ብልጫ ሰጠ፡፡

በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1195 ንዑስ አንቀፅ 1 ላይ በግልፅ እንደተመለከተው የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለሃብትነትን በማወቅ በአስተዳደር ክፍል ለአንድ ሰው የተሰጠ የባለሃብትነት የምስክር ወረቀት ማስረጃ ለተሰጠው ሰው ለዚሁ የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለሃብት እንደሆነ እንደሚያስቆጥረው ተመልክቷል፡፡ በአንፃሩ ማስረጃው የተሰጠው ከደንብ ውጭ በሆነ አሰራር መሆኑ በተረጋገጠ ጊዜ ከፍ ብሎ በፍትሐብሔር ቁጥር 1195 ላይ የተመለከተው የሕሊና ግምት ፈራሸ እንደሚሆን የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1196 (1) ይደነግጋል፡፡ በያዝነው ጉዳይ በሕግ አግባብ ስልጣን ተሰጥቶት ይህን መሰሉን የባለሃብትነት ማስረጃ የሚሰጠው ክፍል ቁጥር 5127386 የሆነው የባለሃብትነት የምስክር ወረቀት የሰረዘው መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ በተሰረዘ የባለሃብትነት ምስክር ወረቀት ደግሞ የሚገኝ የባለሃብትነት መብት አይኖርም፡፡ የተጠሪ ወራሾችም አውራሻቸው ያልነበራቸውን መብት ሊወርሱ አይችሉም፡፡

ለንፅፅር እንዲረዳ በሓሳብ ልዩነት የተሰጠውን አስተያየትና ምክንያት ማየቱ ተገቢ ነው፡፡

አመልካች የአዲስ አበባ መስተዳደር በቤቶቹ ላይ መብት አለኝ የሚለው በመንግስት የተወረሱ ናቸው በሚል መሆኑን መዝገቡ ያስረዳል፡፡ ይሁን እንጂ ቤቶቹ በመንግስት የተወረሱ መሆናቸውን የሚያሳይለት ማስረጃ አላቀረበም፡፡ ለተጠሪዎች አውራሸ ተሰጥቶ የነበረው የባለቤትነት ደብተር ተሰርዟል ማለቱ ብቻውን ለእርሱ መብት የሚሰጠውና አቤቱታውም በፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 358 አግባብ እንዲሰተናገድለት ለማድረግ የሚያስችል አይደለም፡፡ በኔ እምነት የሥር ፍርድ ቤቶች ወደ ዋናው ጉዳይ ተመልሰው ክርክሩን እንደገና መመርመር ሳያስፈልጋቸው አመልካቹን ወደ ክርክሩ ለመግባት የሚያስችልህ መብት መኖሩን አላስረዳህም በሚል ከወዲሁ ጥያቄውን ውድቅ ማድረጋቸው የፈፀሙት የሕግ ስህተት የለም፡፡

የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1195 ግምት በፍ/ሕ/ቁ 1196 በተደነገገው መሠረት ማለትም በሕጉ መሠረት ፈራሸ ሊሆን ይችላል፡፡ የባለቤትነት ካርታው ከደንብ ውጭ የተሰጠ ከሆነ መሰረዙን ህግ ይፈቅዳል፡፡ ሆኖም የመሰረዝ ስልጣን ያለው አካል የካርታው አሰጣጥ ከደንብ ውጭ ስለመሆኑ የማስረዳት ግዴታውን ሊወጣ ይገባል፡፡ የአዲስ አበባ መስተዳደር ሥራና ከተማ ልማት ቢሮ የቤቶች ጉዳይ መምሪያ ካርታውን ሲሰርዝ ካርታው ከደንብ ውጭ የተሰጠ መሆኑን የማሳየትና የማስረዳት ግዴታ አለበት፡፡ ይህን ካላደረገ እርምጃው ከሥልጣን በላይ እንደመሆኑ በሕግ ፊት ዋጋ አይኖረውም፡፡ አመልካች ካርታው ከደንብ ውጭ ስለመሆኑ ወይም ቤቱ በአዋጅ ስለመወረሱ በክርክሩ ቢጠቅስም ከአባባል ያለፈ በተጨባጭ ማስረዳት አልቻለም፡፡ ስለሆነም የመሰረዝ ድርጊቱ የሕጋዊነት መርህን የሚጥስ፣ የሕግ የበላይነትን የሚጻረር፣ ከሥልጣን በላይ የሆነ ድርጊት ነው፡፡

የአብላጫው ድምፅ ይህን መሠረታዊ ጭብጥ አላነሳውም፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ካርታው በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1196 (1) መሠረት ተሰርዞ በምትኩ ለሌላ 3ኛ ወገን ሲተላለፍ ያ ሶስተኛ ወገን የቤቱ ሕጋዊ ባለቤት ስለመሆኑ መረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ የአዲስ አበባ መስተዳድር ባለቤትነቱ የተሰረዘውን የንግድ ቤት የራሱ ሃብት ሲያደርገው በሕጉ መሠረት የባለቤትነት መብት የተሰጠው መሆኑን ማረጋገጥ አለበት፡፡ በአዋጅ ቁ 47/67 ተወርሷል የሚል ከሆነ እንደተወረሰ በበቂ ማስረጃ ማሳየት አለበት፡፡ አመልካች የቤቱ ባለቤት ስለመሆኑ አሁንም በአብላጫው ድምፅ ላይ ጭብጥ ሆኖ ተነስቶ ድምዳሜ ላይ አልተደረሰበትም፡፡ በእርግጥ በተሰረዘ የባለሀብትነት የምስክር ወረቀት የሚገኝ የባለሀብትነት መብት አይኖርም፡፡ ከዚህ ድምዳሜ በፊት ግን የህግ የበላይነት ጥያቄ ምላሽ ማግኘት አለበት፡፡

ተጠሪዎች እየሞገቱ ያሉት የመሰረዙን ሕጋዊነት ነው፡፡ የተጠሪዎች ሙግት በአብላጫው ድምፅ ሰሚ አላገኘም፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ካርታው ከደንብ ውጭ ለአመልካች እንደተሰጠ ስላላስረዳ ድርጊቱ ሕገ ወጥ ወይም ከሥልጣን በላይ ነው፡፡ በቤቱ ላይ በሕጉ መሠረት ባለቤት እንደሆነ ስላላስረዳም ‘ከመሬት ተነስቶ በሌላ ሰው መብት ባለቤትነት ሊኖረው አይችልም፡፡ ይህን ሀሳብ በአነስተኛ ድምፅ አስተያየት ስንቋጨው፤

አመልካች እንኳንስ መብት ሊኖረው ቀድሞውኑ በተቃውሞ ወደ ክርክር ውስጥ እንዲገባ ሊፈቀድለት አይገባም ነበር፡፡

በሌላ ተመሳሳይ መዝገብ እንዲሁ ፍርድ ያረፈበት የባለቤትነት መብት አስተዳደሩ ስላመከነው መና ሆነ ቀርቷል፡፡ በሰ/መ/ቁ. 22719[1] ተጠሪ በሁለት የቤት ባለቤትነት ማረጋገጫ ደብተር /ካርታ/ የተመዘገቡ ሶስት የቤት ቁጥር የተሰጣቸው ቤቶች የራሳቸው መሆናቸው ተረጋግጦ በፍርድ ቤት ውሳኔ አርፎባቸው በአፈጻጸም መዝገብ ቤቶቹን ተረክበዋል፡፡ የፍርድ ሂደቱ እንደተጠናቀቀ አመልካች የቤት ማረጋገጫ ደብተሮቹን በመሰረዙ ተጠሪ ክስ አቀረቡ፡፡ በሰበር ችሎት በነበረው ክርክር ችሎቱ ተጠሪ መብታቸውን በፍርድ ቤት አስከብረውና አረጋግጠው የተፈጸመባቸው ዓይን ያወጣ ህገ ወጥ ተግባር ከማረምና የህግ የበላይነትን ከማስከበር ይልቅ ክስ የማቅረብ መብታቸውን ነፍጓቸዋል፡፡ ችሎቱ ለማመዛን እንደሞከረው፡

አመልካች የተጠሪን የባለቤትነት ማረጋገጫ ሰነዶች ከሰረዘ ተጠሪ አስቀድሞ በተጠቀሱት ቤቶች ላይ ባለመብት መሆኑን የሚያረጋግጡ ማስረጃዎችን በእጁ ማስገባት ይኖርበታል፡፡ ይህ መሠረታዊ ማረጋገጫ ሰነድ ወይም ማስረጃ ሳይኖረው ፍ/ቤት ሰነድ እንዲሰጠው እንዲወሰንለት መጠየቅ አይቻልም፡፡

በአጭር አነጋገር ቤቱን በአስተዳደሩ ህገ ወጥ ተግባር የተነጠቀ ሰው ቤቱ እንዲመለስለት የመጠየቅ መብት እንኳን የለውም፡፡

የሰበር ችሎት ዘግይቶም ቢሆን የሰ/መ/ቁ 17712 እና 22719 ውሳኔ ካገኙ ከሰባትና አምስት ዓመታት በኋላ ፍጹማዊ በሆነውና ፍጹማዊነቱንም ችሎቱ ይሁንታ በሰጠው የአስተዳደሩ ካርታ የማምከን ስልጣን ላይ ገደብ ለማበጀት ተገዷል፡፡ በሰ/መ/ቁ. 42501[2] ፍርድ ባረፈበት ጉዳይ ካርታ ማምከን ህገ ወጥነቱን ጠንከር ባሉ ቃላት እንደሚከተለው ገስጾታል፡፡

አንድ የአስተዳደር አካል በፍርድ ቤት ክርክር መረታቱን ከተረዳ በኃላ በሕጉ የተሰጠውን ስልጣን መነሻ በማድረግ ለፍርዱ መሰጠት መሠረት የሆነውን ማስረጃ ዋጋ በማሣጣቱ ምክንያት የፍርድ አፈፃፀም ዋጋ እንዲያጣ የማድረግ ውጤት በኢ.ፊ.ዲ.ሪ ሕገ መንግስት አንቀጽ 78/1/ እና 79/1/ እና /4/ ስር የተረጋገጠውንና የተከበረውን የነፃ ፍርድ ቤት መኖርንና የዳኝነት ስልጣን ትርጉም አልባ የሚያደርገው ነው፡፡

[1] አመልካች የአ/አ/ ከተማ አስተዳደር ስራ ከተማ ልማት ቢሮ ተተኪ የመሬት ልማትና አስተዳደር ባለስልጣን እና ተጠሪ አቶ ነጋሽ ዱባለ ጥር 14 ቀን 2000 ዓ.ም. ቅጽ 6

[2] አመልካች የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ እና ተጠሪ የአስር አለቃ ደምሴ ዳምጤ ወራሾች /3 ሰዎች/ የካቲት 28 ቀን 2005 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

Draft proclamations

$
0
0

በአስተዳደር ህግ ‘የመጨረሻ ማሰሪያ ድንጋጌ’ (finality clause) ተፈጻሚነትና ውጤት

$
0
0

የኮመን ሎው የአስተዳደር ህግ ስርዓትን በሚከተሉ አገራት (በተለይ በእንግሊዝ) ህግ አውጪው የፍርድ ቤቶችን ስልጣን በህግ ከሚገድብባቸው መንገዶች ዋነኛው በአስተዳደር መስሪያ ቤት ወይም በአስተዳደር ጉባዔ የተሰጠን ውሳኔ የመጨረሻ አድርጎ በማሰር ሲሆን ይህም መደበኛ ፍ/ቤቶች ጥያቄ የተነሳበትን ጉዳይ ድጋሚ እንዳያዩት ስልጣናቸውን ይገድባል፡፡ ያም ሆኖ ግን የእንግሊዝ ፍ/ቤቶች እንደ ማሰሪያ ድንጋጌው (Finality clause) አገላለጽ ከፊል የአቋም ልዩነት ቢያሳዩም በመርህ ደረጃ ግን በህግ የበላይነት ላይ እንደተደረገ ገደብ በመቁጠር የመጨረሻ አስተዳደራዊ ውሳኔዎች ህጋዊነት ከማጣራትና ከመመርመር አልተቆጠቡም፡፡[1]

ህግ አውጪው አንዳንድ አስተዳደራዊ ውሳኔዎች የመጨረሻ እንዲሆኑ ሲደነገግ በህጉ ላይ የተለያዩ አገላለጾችይጠቀማል፡፡ የአገላለጽ መንገዱ መለያየት በተለይ በእንግሊዝ የተለመደ ሲሆን የፍ/ቤቶች ምላሽና ትርጓሜም የህጉን የቋንቋ አጠቃቀም መሰረት ያደርጋል፡፡ በጣም የተለመደው አስተዳደራዊ ውሳኔዎችን የመጨረሻ እንዲሆኑ የማድረግ ዘዴ ‘ውሳኔው የመጨረሻ ይሆናል’ (Shall be final) ወይም ‘ውሳኔው የመጨረሻና የጸና ይሆናል’ (Shall be final and conlusive) የሚል ማሰሪያ ድንጋጌ በማስቀመጥ ነው፡፡

በእንግሊዝ ፍ/ቤቶች ይህን መሰሉ የመጨረሻ ድንጋጌ በአፈፃፀም ወይም በአተረጓጎም ረገድ ቀላል እና የማያሻማ ስለመሆኑ ወጥ ተቋም ተይዞበታል፡፡ በዚህ መሰረት ‘የመጨረሻ’ የሚል ማሰሪያ ድንጋጌ ውጤት የይግባኝ መብትን ከማስቀረት ባለፈ የውሳኔውን ህጋዊነት ከመመርመር አያግድም፡፡ ይህም ማለት ውሳኔው ከይዘት አንፃር እንጂ ህጋዊነቱን በተመለከተ የመጨረሻ ሊሆን አይችልም፡፡

ይህን ሀሳብ የበለጠ ግልጽ ለማድረግ ከአገራችን ህግ ጋር በማነጻጸር እናያለን፡፡ በመንግስትና የግል ሠራተኞች የጡረታ አዋጆች ላይ እንደተመለከተው የመንግስት እና የግል ድርጅት ሰራተኞች ማህበራዊ ዋስትና ኤጀንሲዎች ከጡረታ መበትና ጥቅም ጋር በተያያዘ በየፊናቸው በሚሰጡት ውሣኔ ቅር የተሰኘ ሠራተኛ ቅሬታውን ለማህበራዊ ዋስትና ይግባኝ ሰሚ ጉባዔ የማቅረብ መብት አለው፡፡ የጉባኤው ውሣኔ በፍሬ ነገር ረገድ የመጨረሻ ሲሆን በውሣኔው መሠረታዊ የህግ ስህተት ተፈጽሟል በሚል ቅሬታ ያለው ሠራተኛ የይግባኝ አቤቱታ የሚያቀርበው ለፌ/ጠ/ፍ/ቤት ነው፡፡[2]

የጉባኤው የፍሬ ነገር ውሳኔ የመጨረሻ ተብሎ በፌ/ጠ/ፍ/ቤት የማይመረመረው በህጉ የስልጣን ገደብ ውስጥ የተሰጠ እስከሆነ ድረስ ብቻ ነው፡፡ ለምሳሌ ሚስትነት/ባልነት አስመልክቶ ኤጀንሲው ሆነ ጉባኤው የሚደርስበት መደምደሚያ ከስልጣን በላይ እንደመሆኑ የመጨረሻ አሳሪ ውጤት ሊኖረው አይችልም፡፡ ምክንያቱም ከባልነት/ ሚስትነት ጋር በተያያዘ ውሳኔ ለማሳለፍ ህጉ ስልጣን አልሰጣቸውም፡፡ ይህ የሚያደርሰን ድምዳሜ ‘የመጨረሻ ይሆናል’ የሚል ድንጋጌ ውሳኔው በህግ ከተሰመረው የስልጣን ገደብ ስላለማለፉ ከመመርመር አያግድም፡፡

በአገራችን የመጨረሻ የሚያደርጉ ማሰሪያ አንቀጾች በስፋት የተለመዱ ናቸው፡፡ ለአብነት የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡፡

  • የደህንነት፣ ኢሚግሬሽንና ስደተኞች ጉዳይ ባለስልጣን የውጭ አገር ዜጋንከአገር ለማስወጣት በሚሰጠው ትዕዛዝ ላይ ቅሬታ የሚቀርበው የጠቅላይ ዓቃቤ ህግ እና የባለስልጣኑ ተወካዮች ለሚገኙበት አቤቱታ ሰሚ ኮሚቴ ሲሆን ኮሚቴው ቅሬታውን መርምሮ ለባለስልጣኑ የውሳኔ ሀሳብ ካቀረበ በኋላ ባለስልጣኑ የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ ነው፡፡[3]
  • በፋይናንስ ሪፖርት አዘገጃጀትና አቀራረብ አዋጅ ቁ. 847/2006የተቋቋመው ይግባኝ ሰሚ ጉባዔ ክስ ሰሚዎች (Hearing Examiners) የሚሰጡትን ውሳኔ በይግባኝ አይቶ የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ ነው፡፡[4]
  • የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ወይም አግባብ ያለው ባለሥልጣን አሠሪ፣ የግል ሥራና ሠራተኛ አገናኝ ኤጀንሲ ወኪል ወይም ሠራተኛ የኢትዮጵያ የውጭ አገር ሥራ ስምሪት አዋጅ ቁ. 923/2008እንዲሁም በአዋጁ መሠረት የወጣ ደንብና መመሪያ በመጣሳቸው ምክንያት የሚነሱ አስተዳደራዊ ጉዳዮችን የመስማትና የመወሰን ሥልጣን ያለው ሲሆን በውሳኔው ቅሬታ ያደረበት ወገን ይግባኙን የሚያቀርበው ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ነው፡፡ ፍርድ ቤቱ የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ ነው፡፡[5]
  • የጠቅላይ ዐቃቤ ህግ የምስክር ጥበቃ ተጠቃሚ የሆነ ወይም ያመለከተ ሰው የሚያቀርበውን ቅሬታ ሰምቶ የሚሰጠው ውሳኔ ለፍርድ ቤት አቤቱታ የማይቀርብበት የመጨረሻ ውሳኔ ነው፡፡[6]
  • የራሱንና የቤተሰቡን የገቢ ምንጭ የማሳወቅና የማስመዝገብ ግዴታ ያለበት ሰው የምዝገባ ጊዜ እንዲራዘምለት ለስነ ምግባር መከታተያ ክፍል አቤቱታ አቅርቦ ውድቅ ከተደረገበት ቅሬታውን ለስነ-ምግባርና ፀረ-ሙስናኮሚሽን ማቅረብ የሚችል ሲሆን ኮሚሽኑ በቅሬታው ላይ የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ ነው፡፡[7]
  • የሲቪል አቪየሽን ባለስልጣን የሚወስደውን አስተዳደራዊ እርምጃ በመቃወም አቤቱታ የሚቀርበው ለትራንስፖርት ሚኒስቴርሲሆን የሚኒስቴሩ ውሳኔ የመጨረሻ ነው፡፡[8] ይኸው ሚኒስቴር መ/ቤት የአሽከርካሪ ብቃት ማረጋገጫ ፈቃድ በፈቃድ ሰጪው አካል በመታገዱ ወይም በመሰረዙ ምክንያት የሚቀርብለትን አቤቱታ ምርምሮ የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ ነው፡፡[9] በማሪታይም ዘርፍ አስተዳደር ማፅደቂያ አዋጅ ቁ. 549/199 አንቀጽ 16/ሀ/ ላይ እንዲሁ የሚኒስቴሩ ውሳኔ የመጨረሻ እንዲሆን ተደርጓል፡፡[10]
  • ለማንኛውም እንቅስቃሴ ከግንዛቤ የመነጨ ስምምነት (advance informed agreement) በመከልከሉ ምክንያት እንደገና እንዲታይ የሚቀርብ ማመልከቻ በአዲስ ሳይንሳዊ መረጃ ከተደገፈ እንደ አዲስ ማመልከቻ በድጋሚ ሊታይ ይችላል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ክልከላው የፀና (በእንግሊዝኛው ቅጂ final) ይሆናል፡፡[11]
  • የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ኤጀንሲዋና ዳይሬክተር በሚሰጠው ውሳኔ ላይ የሚቀርበውን ቅሬታ ሰምቶ የመጨረሻ ውሳኔ ለመስጠት ስልጣን ያለው አካል የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ቦርድ ሲሆን የኢትዮጵያ በጎ አድራጎት ድርጅት ወይም ማህበር ጉዳዩ በይግባኝ እንዲታይለት ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቤቱታ ማቅረብ ይችላል፡፡ ይህን መብት በሚፈቅደው አዋጅ ላይ የውጭ አገር የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ተነጥለው ቀርተዋል፡፡[12] ስለሆነም እነዚህን አካላት በተመለከተ የቦርዱ ውሳኔ በዝምታ የመጨረሻ ስለተደረገ ወደ ፍርድ ቤት የመሄጃውን መንገድ ተዘግቷል፡፡

የመጨረሻ የሚለው ቃል በተለያዩ ህጎች ላይ መካተቱ ብቻውን ወደ ፍርድ ቤት ወይም የአስተዳደር ጉባዔ አቤቱታ እንዳይቀርብ አይከለክልም፡፡ የቃሉ አጠቃቀምና አገባብ በጥንቃቄ ሊታይ ይገባዋል፡፡ ለምሳሌ የመንግስት የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ቦርድ ከስልጣንና ተግባራቱ መካከል አንዱ በተቋሙ ውሳኔ (ለምሳሌ በመምህራን ላይ የሚወሰድ የዲሲፕሊን እርምጃ) ላይ ቅሬታ ሲቀርብ መመርመርና የመጨረሻ ውሳኔ መስጠት ነው፡፡[13] የመጨረሻ መሆኑ ግን ውሳኔው በመንግስት ሠራተኞች የአስተዳደር ፍርድ ቤት እንዳይታይ አይገድበውም፡፡ በሰ/መ/ቁ. 78945[14] ተጠሪ በዩኒቨርስቲው ፕሬዚደንት የተወሰደበትን የዲሲፕሊን እርምጃ ቅድሚያ ለቦርድ ሳያቀርብ ለመንግስት ሠራተኞች አስተዳደር ፍርድ ቤት ይግባኝ መጠየቅ እንደማይችል የህግ ትርጉም ተሰጥቷል፡፡ የትርጉሙ እንደምታ በቦርዱ የታየ የተቋሙ ውሳኔ በአስተዳደር ፍርድ ቤቱ መስተናገድ እንደሚችል ነው፡፡

አንዳንድ ጊዜ የመጨረሻ በሚል በተለያዩ ህጎች ላይ የሚጨመረው ማሰሪያ ቃል በይዘቱ በህግ በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ መብት አለመጠየቅ የሚያስከትለውን ውጤት ከመንገር የዘለለ ትርጉም የለውም፡፡ የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለስልጣን የክፍያ መፈጸሚያ የግብይት ፈጻሚ ዕውቅናን በመሰረዝ ወይም በማገድ በሚሰጠው ውሳኔ ላይ ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ የሚቀርበው ውሳኔው በተሰጠ በ30 ቀናት ነው፡፡ በእነዚህ ቀናት ውስጥ ይግባኝ ካልቀረበ ውሳኔው የመጨረሻ ይሆናል፡፡[15] እዚህ ላይ የመጨረሻ የሚለው ሐረግ የሚያመለክተው በጊዜ ገደቡ አቤቱታ ካልቀረበ መብቱ ቀሪ እንደሚሆን ነው፡፡

 

[1] Diane Longley and Rhoda James, ADMINISTRATIVE JUSTICE: CENTRAL ISSUES IN UK AND EUROPEAN ADMINISTRATIVE LAW (Cavendish Publishing Limited, 1999) ገፅ 160

[2] የመንግስት ሠራተኞች ጡረታ አዋጅ ቁጥር 714/2003 አንቀጽ 56/4/ እና የግል ድርጅት ሠራተኞች ጡረታ አዋጅ ቁ. 715/2003 አንቀጽ 55/2/

[3] የኢሚግሬሽን አዋጅ ቁ. 354/1995 አንቀጽ 9 ንዑስ አንቀጽ 1 እና 2

[4] አንቀጽ 48/5/ እና 49/3/

[5] የኢትዮጵያ የውጭ አገር ሥራ ስምሪት አዋጅ 923/2008 አንቀጽ 52 እና 59

[6] የወንጀል ምስክሮችና ጠቋሚዎች ጥበቃ አዋጅ ቁ. 699/2003 አንቀጽ 25/2/

[7] የሀብት ማሳወቂያና ማስመዝገቢያ አዋጅ ቁ. 668/2002 አንቀጽ 8/3/

[8] የሲቪል አቪየሽን አዋጅ ቁ. 616/2001 አንቀጽ 80/1/

[9] የአሽከርካሪ ብቃት ማረጋገጫ ፈቃድ አዋጅ ቁ. 600/2000 አንቀጽ 20/4/

[10] በእርግጥ በአዋጁ የአማርኛ ቅጂ ላይ ውሳኔው የመጨረሻ እንደሚሆን ያልተመለከተ ቢሆንም በእንግሊዝኛው ቅጂ ላይ ግን በግልጽ ‘final decision’ በሚል አገላለጽ ተቀምጧል፡፡

[11] የደህንነተ ሕይወት አዋጅ ቁ. 665/2002 አንቀጽ 15/2/

[12] የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት አዋጅ ቁ. 621/2001 አንቀጽ 104/2/

[13] የከፍተኛ ትምህር አዋጅ ቁ. 650/2001 አንቀጽ 44/1/ ኀ

[14] አመልካች ደብረብርሃን ዩኒቨርስቲ እና ተጠሪ መምህር ባዬ ዋናያ የዳ መስከረም 25 ቀን 2005 ዓ.ም.  ቅጽ  14

[15] የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለስልጣን ለማቋቋም የወጣ አዋጅ ቁ. 551/1999 አንቀጽ 19/3/


Filed under: Articles, Case Comment

ውርስ አጣሪ- የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0

ትርጓሜ

በሟች ንብረት ላይ መብት አለን የሚሉትን ወገኖችን ወይም ወራሾችን የመወሰን፣ የሟች ኑዛዜ መኖር አለመኖሩን የማረጋገጥና በኑዛዜው ተጠቃሚዎችን የመለየት፣ ውርሱን የማስተዳደር የውርሱን ተከፋይ ገንዘብ የመሰብሰብና እዳዎችን የመክፈል፣ የሟች ንብረት ማጣራትና ማፈላለግ እንዲሁም የኑዛዜ ስጦታዎችን የመክፈል ሥልጣን ያለውና እነዚህ ተግባራት እንዲያከናውን በወራሾች ወይም በፍርድ ቤት የሚሾም አጣሪ

ሰ/መ/ቁ. 45905 ቅጽ 11፣[1] ፍ/ህ/ቁ. 944፣ 946፣ 956፣ 960

የአጣሪው ስልጣን ወሰን

በፍ/ብ/ሕ/ቁ. 956 እንደተደነገገው የአጣሪው ሥራ ሟቹ አንድ ኑዛዜ ትቶ እንደሆነ መፈለግና በመጨረሻ ውርሱ የሚደርሳቸው ሰዎች እነማን እንደሆኑ ማረጋገጥ፣ የውርሱን ሃብት ማስተዳደር፣ መክፈያቸው የደረሰውን የውርስ እዳዎች መክፈል እና ሟቹ በኑዛዜ ያደረጋቸውን ስጦታዎች መክፈልና የኑዛዜውን ቃል ለመፈፀም ማንኛቸውም ሌሎች አስፈላጊ ጥንቃቄዎች ማድረግ ነው፡፡ እነዚህ ከዚህ በላይ የተዘረዘሩትን ተግባራት በሚያከናውንበት ጊዜ ደግሞ በኑዛዜው የውርስ ንብረት መሆናቸው ተጠቅሶ የክፍፍል ስርአትም የተቀመጠላቸውና ወራሾች በሙሉ የተስማሙባቸው ንብረቶችና መክፈያቸው የደረሰው የውርስ እዳዎች ሲኖሩ በወራሾቹ ስምምነት መሰረት ንብረቶቹን ሊያከፋፍልና እዳዎችንም ሊከፍል ይችላል፡፡

በኑዛዜው ላይ በተጠቀሱትና ባልተጠቀሱት ንብረቶች የውርስ ሃብት መሆን ያለመሆን ላይ ወራሾቹ ያልተስማሙና ክርክር ያነሱ ከሆነ ግን የአጣሪው ሥራና ሐላፊነት ወራሾች የተስማሙባቸውን ንብረቶች የውርስ ሃብት መሆናቸው መመዝገብ፣ ወራሾች ያልተስማሙባቸው ንብረቶችና እዳዎች ካሉ ደግሞ ማስረጃ በመሰማት ማስረጃው ምን እንደሚያስረዳ ሪፖርቱ ላይ በማስፈር እንዲያጣራ ላዘዘው ፍ/ቤት ማቅረብ እንጂ ንብረት አጣሪው ይህ ንብረት የውርስ ሐብት አይደለም የሚሉ ወራሾች ቢኖሩ ማስረጃ በመስማት የውርስ ሃብት መሆኑን ስለተገነዘብኩኝ ንብረቱ የውርስ ሃብት ነው በማለት ወስኛለሁ ወይም ደግሞ ማስረጃውን እንደተመለከትኩት ንብረቱ የውርስ ሐብት ያለመሆኑን ስላረጋገጥኩኝ የውርስ ሐብት አይደለም በማለት ወስኛለሁ ለማለት የሚያስችለው ሥልጣን የለውም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 23322 ቅጽ 7፣[2] ፍ/ህ/ቁ. 956

የዳኝነት ስልጣን

የአዲስ አበባ እና የድሬዳዋ የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤቶች የወራሽነት የምስክር ወረቀት ከመስጠት በስተቀር ውርስ እንዱጣራ አጣሪ የመሾም የስረ ነገር ሥልጣን የላቸውም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 52530 ቅጽ 11፣[3] ሰ/መ/ቁ. 35657 ቅጽ 9፣[4] አዋጅ ቁ. 361/95 አንቀጽ 41/ለ/ሸ/፣ አዋጅ ቁጥር 408/96

በአብላጫ ድምጽ የተሰጡ

የውርስ አጣሪ ሪፖርት

የውርስ አጣሪው የማጣራቱን ተግባር ከአከናወነ በኋላ ለወራሾችና ለፍርድ ቤት የሚያቀርበው ሪፖርት

በውርስ ሃብት ክፍፍል ረገድ እንደውሳኔ የሚቆጠረው የውርስ አጣሪ ሪፖርት ሳይሆን፣ ሪፖርቱ በሕጉ መሠረት የቀረበ ነው በሚል በፍ/ቤት የሚሰጠው ውሳኔ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ 44038 ያልታተመ[5]

የውርስ አጣሪ ሪፖርት በፍርድ ቤት መጽደቅ በራሱ ፍርድ ሁኖ ለአፈፃፀም የሚቀርብ ሣይሆን እንደማስረጃ የሚያገለግል ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 45905 ቅጽ 11፣[6] ፍ/ህ/ቁ. 944፣ 946፣ 956፣ 960

[1] አመልካች ሚስስ ሚላን ፑሲጂ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ እነ ሐንድሬ ፒስ ማልጂ /2 ሰዎች/ ጥቅምት 3 ቀን 2003 ዓ.ም.

[2] አመልካች ወ/ሮ አዳነች ወርዶፋ እና ተጠሪዎች እነ ወ/ሮ አስናቀች ወርዶፋ ሰኔ 19 ቀን 2000 ዓ.ም.

[3] አመልካች እነ አቶ ሰናይ ልዑልሰገድ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ ትእግስት ኃይሌ   ኅዳር 14 ቀን 2003 ዓ.ም.

[4] አመልካቾች እነ ወ/ሮ እመቤት መክብብ እና ተጠሪ አቶ በድሉ መክብብ ጥቅምት 06 ቀን 2001 ዓ.ም.

[5] አመልካቾች እነ ጌታቸው ደስታ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ በላይ መለሰ የካቲት 9 ቀን 2002 ዓ.ም.

[6] አመልካች ሚስስ ሚላን ፑሲጂ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ እነ ሐንድሬ ፒስ ማልጂ /2 ሰዎች/ ጥቅምት 3 ቀን 2003 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

የእምነት ቃል —የሰበር ችሎት የህግ ትርጉም

$
0
0

በወንጀል ተጠርጣሪ ግለሰብ በምርመራ ሂደት ወይም ደግሞ ተከሳሽ በክሱ ሂደት የራሱን አጥፊነት በመቀበል የሚሰጠው ቃል

አንድ ተጠርጣሪ ወይም ተከሳሽ በምርመራ ሂደትም ሆነ ክስ ከቀረበበት በኃላ ክሱን ለሚሰማው ፍርድ ቤት የሚሰጠው የእምነት ቃል በሕግ ተቀባይነት ካላቸው የማስረጃ ዓይነቶች ውስጥ የሚካተት መሆኑ በወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 27፣ 35 እና 134 ድንጋጌዎች ተመልክቷል፡፡ ተጠርጣሪው ወይም ተከሳሹ የዚህ ዓይነቱን የእምነት ቃል የሚሰጠው የራሱን አጥፊነት አምኖ በመቀበል እንደሆነ የሚገመት በመሆኑ ሌሎች ተጠርጣሪዎች፣ ተከሳሾች ወይም ማናቸውም ሌላ ሰው በወንጀሉ አደራረግ ውስጥ ተሳትፎ የነበራቸው ስለመሆኑ ወይም ስላለመሆኑ በእምነት ቃሉ ውስጥ የሚገልጻቸው ፍሬ ነገሮች ምናልባት ለቀጣይ ምርመራ ፍንጭ ሊሰጡ ይችሉ ይሆናል ከሚባል በቀር በማናቸውም ሰው ላይ አሉታዊም ሆነ አዎንታዊ ሕጋዊ ውጤት ሊያስከትሉ የሚችሉ ተደርገው ሊወሰዱ የሚችሉበት የሕግ አግባብ የለም፡፡

በሌላ አነጋገር አንድ ተጠርጣሪ ወይም ተከሳሽ በምርመራ ሂደትም ሆነ ክሱን ለሚሰማው ፍርድ ቤት የሚሰጠው የእምነት ቃል ውጤት በራሱ በቃል ሰጪው ላይ ተወስኖ የሚቀር ከመሆኑ ውጪ ወደሌሎች ተጠርጣሪዎች ወይም ተከሳሾች ሊተላለፍ የሚችል አለመሆኑን ከላይ ከተጠቀሱት ድንጋጌዎች አነጋገር እና ይዘት መገንዘብ የሚቻል ከመሆኑም በላይ ወንጀሉን የፈጸሙት በጋራ ወይም በመተባበር መሆኑን በማመን አንደኛው ተከሳሽ የሚሰጠው የእምነት ቃል ወንጀሉን አልፈጸምኩም በማለት ክዶ በሚከራከረው ሌላኛው ተከሳሽ ላይ ሕጋዊ ውጤት ሊያስከትል የማይችል ስለመሆኑ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት በመዝገብ ቁጥር 94450 በ25/07/2006 ዓ.ም. የሰጠው አስገዳጅ የሕግ ትርጉም በተያዘው ጉዳይ ላይ ተፈጻሚነት ያለው መሆኑን ተገንዝበናል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 96310 ቅጽ 17፣[1] ወ/መ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 27፣35 እና 134

በወንጀል ጉዳይ በወ/መ/ሕ/ሥ/ሥ/ቁ. 134(1) እንደተደነገገው ተከሣሹ የተከሰበበትን የወንጀል ክስ ይዘት በሚገባ ተረድቶ አድራጐቱን እንደቀረበበት የወንጀል ክስ ዝርዝር መፈፀሙን አምኖ የእምነት ቃል በሰጠ ጊዜ ይህ የእምነት ቃል ለቀረበበት የወንጀል ክስ ማስረጃ ሆኖ በዚሁ ማስረጃ መሠረት የጥፋተኝነት ውሣኔ መስጠት የሚቻልበት ሥርዓት ተደንግጓል፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ አኳኋን ተከሣሹ የሚሰጠው የእምነት ቃል በማስረጃነቱ ተይዞ የሚሰጠው የጥፋተኛነት ውሣኔ ውሣኔውን በሰጠው ፍ/ቤቱ ብቻ ተወስኖ የሚቀር አይደለም፡፡ በዚህ ውሣኔ ቅሬታ የተሰማው ወገን በህገ-መንግስቱም አንቀጽ 20(6) ሆነ በዝርዝር በወ/መ/ሕ/ሥ/ሥ/ሕጉ መሠረት ከታች ወደ ላይ በይግባኝ የመከራከር መብቱን ለማስጠበቅ የይግባኝ አቤቱታ የሚያቀርብበት ሥርዓት ተዘርግቷል፡፡

በዚህ መሠረት በይግባኝ በሚቀርበው መከራከሪያ ነጥብነቱ እንደ ወ/መ/ሕ/ሥ/ሥ/ቁ. 134(1) ድንጋጌ አነጋገር የወንጀሉን አድራጐት ለመፈፀሙ የእምነት ቃል አልሰጠሁም፤ ነገር ግን እንዳመንኩ ተደርጎ ጥፋተኛ ነህ ተብያለሁ በማለት ቅሬታ የቀረበ እንደሆነ ተከሳሹ ተላልፎታል በሚል የተጠቀሠበት ድንጋጌ ሥር የተቋቋመውን የወንጀል ዝርዝር ተከሣሹ በአፈፃፀሙ ረገድ የሰጠውን ዝርዝር የአፈፃፀም ሁኔታ በማገናዘብ በእርግጥም እንደ ክሱ የወንጀሉን አድራጐት ፈጽሞታል ወይስ አልፈፀመውም የሚለውን ለመለየት ተከሣሹ ሰጠ የተባለው ዝርዝር የእምነት ቃል በመዝገቡ ላይ ሠፍሮ ካልተገኘ በቀር የበላይ ፍ/ቤቶች ተገቢውን ዳኝነት ለመስጠት አያስችላቸውም፡፡

ሰ/መ/ቁ 77842 ቅጽ 14፣[2] ወ/መ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 134/2/

በወንጀል የተከሰሰ ሰው ጥፋተኛ ተብሎ የሚቀጣው በወ/መ/ሥ/ሥ/ሕግ ቁጥር 134(1) መሠረት በሰጠው የእምነት ቃል መሰረት ከሆነ ፍርድ ቤቶች ተከሳሹ ከሰጠው የእምነት ቃል ውስጥ ተከሳሹን የሚጠቅመውን ክፍል በመተው፤ በዕምነት ቃሉ ያላስመዘገበውን ፍሬ ነገር መሰረት በማድረግ ቅጣት ሊያከብዱ አይገባም፡፡

ሰ/መ/ቁ 96954 ቅጽ 16[3]

[1] አመልካች አቶ ጉዲና ለማ ገዛኸኝ እና ተጠሪ የደቡብ ብ/ብ/ሕ/ክ/መንግስት የስ/ፀ/ሙስና ኮሚሽን ዐ/ሕግ ህዳር 26 ቀን 2007 ዓ.ም.

[2] አመልካች አቶ ሳሚ ሁሴን እና ተጠሪ የፌደራል ዐቃቤ ህግ ታህሣስ 03 ቀን 2005 ዓ.ም.

[3] አመልካች ዘፈሩ ወልደ ትንሣኤ አብርሃ እና ተጠሪ የፌዴራል ዐቃቤ ህግ ሚያዚያ 24 ቀን 2006 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

Non-Judicial Review in Ethiopia: Constitutional Paradigm, Premise and Precinct|K. I. Vibhute

Legality Principle of Taxation in Ethiopia: At the State of Porosity or its Non-Existent from Inception?|Alekaw Assefa Dargie

Safety manual for public servants Against poignant prosecutions|Yohannes Woldegebriel in response to የወንጀል ህግ አንቀጽ 23

Submit posts to Ethiopian Legal Brief

A DRAFT PROCLAMATION TO PROVIDE FOR THE PUBLIC PRIVATE PARTNERSHIP

Viewing all 992 articles
Browse latest View live


<script src="https://jsc.adskeeper.com/r/s/rssing.com.1596347.js" async> </script>