chilot.me ብሎግን ከመጀመሬ በፊት ‘በላልበልሃ’ የተባለ ብሎግ ላይ የተለያዩ አዝናኝና አስተማሪ የህግ ጽሑፎች ሳወጣ እንደነበር የድረ ገፁ ጎብኚዎች የምታስታውሱት ነው፡፡ ‘በላልበልሃ’ ከተዘጋ ጥቂት ዓመታት አልፈውታል፡፡ ሆኖም በዛ ላይ ሲወጡ የነበሩ አዝናኝና አስተማሪ ጽሑፎች በተለይም የችሎት ገጠመኞችና ቀልዶች፣ አስገራሚ ክሶችና ፍርዶች፣ የጠበቃ ቀልዶች፣ ህግ ነክ ጥቅሶች፣ አስገራሚ ህጎች እና ሌሎችም አዳዲስ ተጨማሪ ጽሑፎች ታክሎባቸው ‘ህግ ቀልድና ቁምነገር’ በሚል በመጽሐፍ ታትመዋል፡፡
‘ህግ ቀልድና ቁምነገር’ የሚለው መጽሐፍ ዋጋው 36 ብር ሲሆን በዩኒቨርሳል የመጽሐፍት መደብር (አዲስ አበባ 4 ኪሎ) እና በሁሉም የሜጋ የመጽሐፍት መደብሮች ያገኙታል፡፡
በመጽሐፉ ዙሪያ ከጀርመን ሬዲዮ ጣቢያ የአማርኛ ዝግጅት ክፍል ጋር ያደረግኩትን ቃለ መጠይቅ ለማዳመጥ እዚህ ላይ ይጫኑ፡፡
ከዚህ በታች የቀረቡት ጽሑፎች የተወሰዱት ከመጽሐፉ ሲሆን መጽሐፉን ገዝታችሁ ታነቡ ዘንድ እጋብዛለው፡፡
የጠበቃ፣ የዓቃቤ ህግና የችሎት ቀልዶች
አንድ ጠበቃ በጣም አርጅቶ ከሞተ በኋላ አንድ ሰው ማንነቱን ደብቆ ጠበቃውን ማናገር እንደሚፈልግ በመግለፅ በተደጋጋሚ ወደ ጠበቃው ቢሮ ስልክ ይደውላል፡፡ የፀሐፊዋ የዘወትር ምላሽ “ይቅርታ ጌታዬ! ሞቷል!” የሚል ነበር፡፡ ሆኖም ደዋዩ መደወሉን አላቋረጠም፡፡ በመጨረሻም በነገሩ ግራ የተጋባችው ፀሐፊ የደዋዩ ድምጽ አንድ መሆኑን ስትረዳ ማን እንደሆነና ለምን በተደጋጋሚ እንደሚደውል ትጠይቀዋለች፡፡
የደዋዩ ምላሽ—-“የሱ ረዳት ነበርኩኝ፡፡ በተደጋጋሚ “ሞቷል!” የሚለውን ቃል ስሰማ እንዴት አንጀቴ ይርሳል መሰለሽ፡፡”
* * *
አንድ ጀማሪ ጠበቃ ወደቢሮው ባለጉዳይ እየመጣ መሆኑን በመስኮት ተመለከተና ገበያውን ለማዋደድ ጠረጴዛ ላይ ያለውን የመስመር ስልክ አንስቶ ማውራት ጀመረ፡፡
“ይቅርታ ያድርጉልኝ ጌታዬ! መዝገብ በመዝገብ ተደራርቦብኝ በስራ ጫና ተወጥሬአለሁ፡፡ የእርስዎን ጉዳይ ለማየት ቢያንስ የአንድ ወር ጊዜ ያስፈልገኛል፡፡”
በመቀጠል ስልኩን ዘጋና ቀና ብሎ ፊት ለፊቱ ተገትሮ የሚጠብቀውን ባለጉዳይ “እሺ ምን ልርዳዎት ጌታዬ?” ሲል ጠየቀው፡፡
ሰውየውም “ምንም! የተቆረጠውን ስልክዎትን ለመቀጠል ከቴሌ ነው የመጣሁት!”
* * *
የተከሳሽ ጠበቃ የመከላከያ መልሱን ለማሻሻል አቤቱታ ቢያቀርብም በስነ ስርዓት ህጉ መሰረት የክስ አቤቱታ እንጂ የመከላከያ መልስ ማሻሻል አይፈቀድም በሚል ምክንያት ውድቅ ተደረገበት፡፡ ጠበቃው በዳኛው አላዋቂነት በግኗል፡፡
ዳኛው ትዕዛዙን አንብበው እንደጨረሱ ጠበቃው “ጌታዬ!” አለና ዲስኩሩን ጀመረ፡፡ “ጌታዬ እኔ እርስዎን ጠማማ ብዬ ብጠራዎት ምን ያደርጋሉ?”
ዳኛው በተራቸው በገኑ፡፡ “ምን አልክ አንተ? ሞክረኛ! በችሎት መድፈር የእጅህን አቀምስህና ፈቃድህ እንዲሰረዝ አደርጋለው፡፡” “ቃል ሳይወጣኝ እንደዛ ኖት ብዬ ባስብስ?” ጠበቃው መልሶ ጠየቀ፡፡ “እንደዛ ከሆነ ምንም ማድረግ አልችልም፡፡ የፈለግከውን የማሰብ መብትና ነጻነት አለህ፡፡” ዳኛው ተረጋግተው አረጋጉት፡፡
“እንግዲያውስ ጌታዬ! እርስዎ ጠማማ ኖት ብዬ እንዳሰብኩኝ በመዝገቡ ላይ ይመዝገብልኝ!”
* * *
ዳኛው ተከሳሹን “ፍርድ ቤት ተከላካይ ጠበቃ እንዲያቆምልህ ትፈልጋለህ?” ሲሉ ይጠይቁታል፡፡
ተከሳሽ——“አይ በራሴ ብከራከር እመርጣለሁ፡፡ የቀረበብኝ ክስ እኮ በጣም ከባድ ነው!”
* * *
አንድ ሰው ኒዮርክ ከተማ ውስጥ በሐሰት ጠበቃ ነኝ እያለ በማታለል በፍርድ ቤት በተደጋጋሚ ከቀረበ በኋላ ተደርሶበት በፈፀመው የማጭበርበር ወንጀል ክስ ቀርቦበት ጥፋተኛ ተብሎ ዘብጥያ ይወርዳል፡፡ ታሪኩ በእርግጥ ያጋጠመ ሲሆን በወቅቱ የብዙዎችን ትኩረት ስቦ ነበር፡፡ ታዲያ በየቀኑ በእሳቸው ፊት ሲቀርብ አንዴም ያልጠረጠሩት ዳኛ “ጠበቃ እንዳልሆነ መጠርጠር ነበረብኝ፡፡ ሁል ጊዜ ቀጠሮ አክባሪና ትሁት ነው” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡
* * *
የተከበሩት ዳኛ በጥቁሩ ካባቸው ደምቀው በችሎት አስከባሪ ፖሊስ ታጅበው ወደ ችሎት ሲገቡ ፖሊሱ ገና “አንዴ ተነሱ!” ብሎ ተናግሮ ሳይጨርስ በአዳራሽ የነበረው ሁሉ ብድግ ብሎ አከበራቸው፡፡ “ተቀመጡ!” አሉና የመጀመሪያውን መዝገብ ገልጠው ከሳሽና ተከሳሽን ተጣሩ፡፡ በመቀጠል የግራ ቀኙ ጠበቆች ብድግ ብለው በየተራ ስማቸውን አስመዘገቡ፡፡
ዳኛው በችሎት አዳራሽ የተሰበሰበውን ባለጉዳይ አንዴ አየት አደረጉና ወደ ጠበቆቹ ዞረው በትኩረት እየተመለከቱ “በዚህ ጉዳይ የከሳሽና የተከሳሽ ጠበቆች የሰጣችሁን ጉቦ ደርሶኛል” በማለት ተናገሩ፡፡ ይሄኔ ጠበቆቹ በሐፍረት እርስ በእርስ መተያየት ጀመሩ፡፡
“የከሳሽ ጠበቃ የሰጠኝ 15 ሺ ብር ሲሆን የተከሳሽ ጠበቃ ደግሞ 10 ሺ ብር ሰጥቶኛል፡፡” ዳኛው ይህን ከተናገሩ በኋላ ከኪሳቸው ቼክ አውጥተው ለከሳሽ ጠበቃ የሚከፈል 5 ሺ ብር ከጻፉ በኋላ “የከሳሽ ጠበቃ 5 ሺ ብር እላፊ ሰጥተኸኛል፡፡ እንካ ቼኩን ተቀበል፡፡” ብለው ቼኩን ሰጡት፡፡ ጠበቃው እያላበው ቼኩን ተቀበለ፡፡
በመጨረሻም ዳኛው ፊታቸው ላይ እፎይታና እርጋታ እየተነበበ እንዲህ አሉ፡፡
“አሁን ችሎቱ የእናንተን ጉዳይ ያለ አድልዎ ገለልተኛ ሆኖ ማየቱን ይቀጥላል፡፡”
* * *
ከግራ ወደቀኝ እየተመላለሰ ባለማቋረጥ ለረጅም ጊዜ ክርክሩን በማቅረብ ላይ ያለ አንድ ሞቅ ያለው ጠበቃ በክርክሩ መሐል ቆም ብሎ “እየተከተሉኝ ነው ጌታዬ?” ሲል ዳኛውን ይጠይቃቸዋል፡፡ ዳኛውም “አዎ በቅርበት እተከተልኩህ ነው፡፡ ግን ግራ የገባኝ ነገር ወዴት ነው የምትሄደው?” በማለት መልሰው በነገር ጠቅ አድርገውታል፡፡
* * *
አንድ ሰው በጁሪ (jury) አባልነት እንዲያገለግል ከተመረጠ በኋላ በችሎት ላለመገኘት የተለያዩ ምክንያቶችን ቢደረድርም ሁሉም አጥጋቢና አሳማኝ ሆነው ባለመገኘታቸው በተደጋጋሚ ያቀረበው ጥያቄው ውድቅ ይደረግበታል፡፡
የቀጠሮው ቀን ሲደርስ ዕድሉን እያማረረ በችሎት ተገኘ፡፡ አሁንም ቢሆን ግን ተስፋ አልቆረጠም፡፡ የመጨረሻ ዕድሉን ለመሞከር ወሰነ፡፡ እናም ችሎቱ ሊጀመር ሲል ብድግ ብሎ መናገር እንዲፈቀድለት አሳሰበ፡፡
“ጌታዬ! በዚህ ጁሪ በአባልነት መቀጠል የምችል አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም በተከሳሹ ላይ ነጻ እና ፍትሐዊ ዳኝነት እሰጣለው ብዬ አላምንም፡፡ ይሄን ተከሳሽ እንዲሁ አፍጥጬ ሳየው ‘በቃ! ይሄ መሰሪ ራሰ በራ ወንጀለኛው ራሱ ነው!’ ብዬ ደመደምኩኝ፡፡ በመነጽር ውስጥ የተደበቁትን ተንኮል ያዘሉ ዓይኖቹን ሳየቸውማ የወንጀሉ ፈጻሚ ራሱ ስለመሆኑ ቅንጣት ጥርጣሬ አላደረብኝም፡፡ ታዲያ ጌታዬ እንዲህ ዓይነት የተዛባ እምነት ኖሮኝ እንዴት በአባልነት ልቀጥል እችላለው፡፡ ስለሆነም ችሎቱ ያሰናብተኝ፡፡”
ዳኛው አቤቱታውን በጥሞና ከሰሙ በኋላ “አርፈህ ቁጭ በል! እሱ ዓቃቤ ህጉ ነው፡፡”
Filed under: Uncategorized
